አዲስ አበባ፣ የካቲት 28፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) የኢትዮጵያ አየር ሃይል በሶማሊያ ሸበሌ ዞን በሚገኙ የአል ሸባብ ይዞታዎች ላይ የአየር ጥቃት መፈፀሙን የሶማሊያ መከላከያ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
የሶማሊያ መከላከያ ሚኒስትር አብዱልቃድር ሞሃመድ እንዳሉት÷የኢትዮጵያና ሶማሊያ አየር ሃይሎች ለሰዓታት በወሰዱት መጠነ ሰፊ የአየር ጥቃት የሽብር ቡድኑ በቅርቡ የሶማሊያ ብሔራዊ ጦርን በድንገት በማጥቃት የተቆጣጠራትን የማዕከላዊ ሸበሌ ከተማ ማስለቀቅ ተችሏል፡፡
የኢትዮጵያ አየር ሃይል አል ሸባብ ላይ የወሰደው የአየር ጥቃት በሁለቱ ሀገራት ትብብር መሆኑንም ነው የገለጹት፡፡
በቡድኑ ላይ የተወሰደው ጥቃት አልሻባብ በተለያዩ ከተሞቸ የሚያደርገውን መስፋፋት ያስቆማል የተባለ ሲሆን÷የቡድኑን አደረጃጀት እንደሚያዳክምም ተገልጿል፡፡
የአንካራውን ስምምነት ተከትሎ ሁለቱ ሀገራት በደህንነት ጉዳዮች ላይ ያላቸው ትብብር እያደገ መምጣቱን ያነሱት ሚኒስትሩ÷ ኢትዮጵያ በአል ሸባብ ይዞታዎች ላይ የፈጸመቸው ጥቃትም ለዚህ ማሳያ ነው ብለዋል፡፡
የተቀናጀ ርምጃው እንደ አልሸባብ ያሉ ዓለም አቀፍ የሽብር ቡድኖችን ለማዳከም ቀጣናዊ እና የሁለትዮሽ ትብብር አስፈላጊ መሆኑን የተገነዘብንበት ነው ሲሉ መጥቀሳቸውን ጋሮዌ ኦንላይን ዘግቧል፡፡
በቅርቡ የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ሀሰን ሼክ መሀሙድ አዲስ አበባ መጥተው ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ጋር የሁለትዮሽ ግንኙነትን ማጠናከር የሚያስችል ውይይት ማድረጋቸው ይታወቃል፡፡
በተመሳሳይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ወደ ሶማሊያ አቅንተው ከሶማሊያ ፕሬዚዳንት ሀሰን ሼክ መሀሙድ ጋር በተለያዩ ጉዳዮች ላይ መምከራቸው ይታወሳል፡፡
በውይይታቸውም በሰላምና ጸጥታ፣ ኢኮኖሚ፣ ዲፕሎማሲ እና የተቀናጀ መሰረተ-ልማት ግንባታን ጨምሮ በሌሎች ጉዳዮች ላይ መክረዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ “ቀጣናዊ ትስስር የጋራ ህልማችንን እውን ለማድረግ እጅግ ጠቃሚ ነው፤ ለጋራ እድገታችን ልንጠቀምበት የምንችል ትልቅ አቅም አለን፤ በተናጠል ማደግ አንችልም፤ በጋራ ስንቆም ጠንካራ ነገ እና ብሩህ ተስፋ ይኖረናል “ ሲሉ መግለጻቸው የሚታወስ ነው፡፡
የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ሀሰን ሼክ መሀሙድ በበኩላቸው÷ቀጣናዊ ትብብር ቁልፍ መሆኑን አጽንኦት በመስጠት በትብብር መስራት ከምንጊዜውም በላይ አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል፡፡
በአቤል ንዋይ እና ሚኪያስ አየለ