Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

 ኢትዮጵያ በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ዘርፍ ግምባር ቀደም ሀገር እየሆነች ትገኛለች – ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 9፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ኢትዮጵያ በአርቴፊሻል ኢንተሊጀንስ፣ በዲጂታል መሠረተ ልማት እና በክሕሎት ማበልጸጊያ ሥራዎች አርአያ እየሆነች መምጣቷን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ “አርቴፊሻል ኢንተለጀንስን ለአፍሪካ ብልጽግና እና ትብብር” በሚል መሪ ሃሳብ እየተካሄደ ባለው የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ለአፍሪካ መድረክ ላይ ተሳተፈዋል፡፡

በመድረኩ ባደረጉት ንግግርም አፍሪካ በሀገር በቀል የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ የተመራ አካታች ብልጽግና በማምጣት የአጀንዳ 2063 ግቦችን ለማሳካት እየሰራች መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡

ኢትዮጵያም በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ፣ በዲጂታል መሠረተ ልማት እና በክሕሎት ማበልጸጊያ ሥራዎች ግምባር ቀደም ሀገር እየሆነች መምጣቷን ነው የገለጹት፡፡

በኢትዮጵያ የተጀመሩ የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት፣ ዲጂታል መታወቂያ እንዲሁም የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ስልጠና የኢትዮጵያን የዲጂታል ሕልሞች ወደ ተጨባጭ ለውጥ የሚቀየሩ ናቸው ብለዋል፡፡

አፍሪካ በ2030 አርቴፊሻል ኢንተለጀንስን በሥነ ምግባር እና በአካታችነት መርሕ በአህጉራዊ መልክ ልትገነባ እንደሚገባ አጽንኦት መስጠታቸውንም የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት መረጃ ያመላክታል፡፡

Exit mobile version