Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

ኢትዮጵያ ስደተኞችን ተቀብላ በማስተናገድ እያከናወነች ያለው ተግባር የሚደነቅ ነው

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 6፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ኢትዮጵያ ስደተኞችን ተቀብላ በማስተናገድ እያከናወነች ያለው ተግባር እና ጥረት የሚደነቅ ነው አሉ የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ።

ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀ ሥላሴ ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲን በብሔራዊ ቤተመንግስት ተቀብለው አነጋግረዋል።

ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ ከውይይቱ በኋላ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ በርካታ ስደተኞችን ተቀብላ በማስተናገድ ላይ ትገኛለች።

በአሁኑ ወቅትም ከደቡብ ሱዳን፣ ሱዳን እና ከሌሎች ሀገራት ስደተኞችን እየተቀበለች መሆኑን አንስተዋል።

ኢትዮጵያ ስደተኞችን ተቀብላ በማስተናገድ እያከናወነች ያለው ተግባርና ጥረት የሚደነቅ መሆኑን ገልጸው፤ ለዚህም የሚደረገው ድጋፍ እንደሚጠናከር ማረጋገጣቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

ከዚህ በተጨማሪ ስደተኞችን ከመቀበል እና ከማስተናገድ አንጻር የኢትዮጵያን መልካም ተግባር ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ እንዲያውቀውና ድጋፍ እንዲያደርግ በትኩረት ይሰራል ብለዋል።

ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀ ሥላሴ እና የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ ያደረጉት ውይይት ፍሬያማ እንደነበር ውይይቱን የተከታተሉት የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ጠይባ ሀሰን አስታውቀዋል።

በተለይ በኢትዮጵያ በሚገኙ ስደተኞች ዙሪያ እንዲሁም ለስደተኞች ድጋፍ በሚጠናከርበትና በተያያዥ ጉዳዮች ላይ ሰፊ ውይይት አድርገዋል ብለዋል።

Exit mobile version