Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በከተሞች ለማስፋፋት በትኩረት ይሰራል – ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)

‎አዲስ አበባ፣ መስከረም 3፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዲጂታል ቴክኖሎጂን ጥቅም ላይ በማዋል ቀልጣፍ አገልግሎት መስጠት ያስችላል አሉ ‎የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ፡፡

‎ርዕሰ መስተዳድሩ የሚዛን አማን መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ማዕከል ግንባታ ያለበትን ደረጃ ተመልክተዋል፡፡

‎የአማን መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ግንባታ ሥራ በተያዘው መስከረም ወር መጨረሻ ተጠናቅቆ ለአገልግሎት እንደሚበቃ ተመላክቷል፡፡

ማዕከሉ በአንድ ጊዜ 32 አገልግሎቶችን በአንድ ማዕከል የመስጠት አቅም ያለው ሲሆን÷ ዲጂታል ኢትዮጵያን ዕውን ለማድረግ የተያዘው ራዕይ አንድ አካል ነው።

ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) የሚዛን አማን መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስከረም ወር መገባደጃ ላይ አገልግሎት እንዲሰጥ ለማድረግ አስፈላጊው ጥረት እየተደረገ ነው ብለዋል።

‎ማዕከሉ አገልግሎት መስጠት ሲጀምር ከተገልጋዮች ዘንድ የሚነሱ የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን እና እንግልቶችን መፍትሄ ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል።

‎ከዚህ ባለፈም ከእጅ ንኪኪ ነጻ የሆነ ዲጂታል አገልግሎትን በማሳለጥ የሚስተዋሉ ሙስናና ብልሹ አሰራሮችን መቅረፍ እንደሚያስችል ታምኖበታል፡፡

‎ርዕሰ መስተዳድሩ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በቀጣይ በክልሉ ክላስተር ከተሞች የማስፋፋቱ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል፡፡

‌‎በፍሬው ዓለማየሁ

Exit mobile version