አዲስ አበባ፣ ሕዳር 2፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በሀረሪ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በዛሬው ዕለት ተመርቆ ስራ ጀምሯል።
የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ እና የሲቪል ሰርቪስ ምክትል ኮሚሽነር አልማዝ መሰለ ማዕከሉን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል።
በማዕከሉ ሰባት የክልሉና የፌደራል ተቋማት የተካተቱ ሲሆን፥ ከ20 በላይ አገልግሎቶችን በአንድ ቦታ ለመስጠት ያስችላል።
ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት ማዕከሉ ፍትሃዊና ጊዜውን የዋጀ የመንግስት አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል፡፡
የሐረሪ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በብቁ የሰው ኃይልና በቴክኖሎጂ ተደራጅቶ ወደ ስራ መግባቱን ገልጸው፥ የተቀናጀ አገልግሎት በመስጠት የመልካም አስተዳደር ችግርና ብልሹ አሰራርን ለመቀነስ ያግዛል ብለዋል።
በክልሉ በወረዳ ጀምሮ የህዝብን ፍላጎት መነሻ ባደረገ መልኩ የአገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል እንደሚሰራ የገለጹት ርዕሰ መስተዳድሩ፥ በዚህ ረገድ ማዕከሉ በተለይም እንግልትን ለማስቀረት ከፍተኛ ፋይዳ ይኖረዋል ነው ያሉት፡፡
የሲቪል ሰርቪስ ምክትል ኮሚሽነር አልማዝ መሰለ በበኩላቸው፥ በሀገሪቱ ወደ አገልግሎት የገቡ ማዕከላት ፍትሃዊና ፈጣን አገልግሎት በመስጠት ረገድ ተጨባጭ ውጤት እያመጡ ይገኛሉ ብለዋል።
በዛሬው እለት የተመረቀው የሐረሪ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ጨምሮ በአጠቃላይ በሀገሪቱ አገልግሎት መስጠት የጀመሩ ማዕከላት ቀጥር 18 መድረሳቸውን ነው የጠቆሙት።
በቀጣይም እንደሀገር መሶብ የአንድ ማዕከላትን ቁጥር ወደ 100 በማድረስ የአገልግሎትን ልህቀት ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል።
በተስፋዬ ኃይሉ

