አዲስ አበባ፣ የካቲት 2፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ እድገት ለማስቀጠል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ሚና የጎላ ነው አሉ የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ።
በሳዑዲ አረቢያ እና በዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም (አይኤምኤፍ) ትብብር የተዘጋጀውና በፍጥነት በማደግ ላይ ባሉ ሀገራት ኢኮኖሚ ላይ ያተኮረው ጉባኤ እየተካሄደ ነው።
ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) በጉባኤው ላይ እንዳሉት፥ ኢትዮጵያ የተገበረችው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ለኢኮኖሚ እድገቷ ወሳኝ ሚና እየተጫወተ ይገኛል፡፡
የኢኮኖሚ እድገትን ለማስቀጠል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያዎች የጎላ ሚና እንዳላቸው ጠቅሰው፥ ለዚህም ኢትዮጵያ ተግባራዊ ባደረገችው ማሻሻያ ያስመዘገበቻቸው እድገቶች ማሳያ ናቸው ብለዋል፡፡
በዘንድሮው በጀት ዓመት ኢትዮጵያ ባለሁለት አሃዝ የኢኮኖሚ ዕድገት ለማስመዝገብ በትኩረት እየሰራች መሆኗን አንስተዋል፡፡
በጉባኤው ላይ የተለያዩ ሀገራት የፋይናንስ ሚኒስትሮችና የማዕከላዊ ባንክ ገዥዎችን ጨምሮ ከግሉ ዘርፍ የተውጣጡ ዓለም አቀፍ መሪዎች ኢኮኖሚያቸው በፍጥነት በማደግ ላይ ባሉ ሀገራት ቀጣይ ሁኔታ ላይ እየመከሩ ይገኛሉ፡፡
በሶስና አለማየሁ

