አዲስ አበባ፣ የካቲት 18፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀ ሥላሴ ከእስራኤል ፕሬዚዳንት አይዛክ ሄርዞግ ጋር ተወያይተዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ታዬ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መረጃ÷ ዛሬ ወደ ኢትዮጵያ ለይፋዊ ጉብኝት ከመጡት የእስራኤል ፕሬዚዳንት አይዛክ ሄርዞግ ጋር መወያየታቸውን ገልጸዋል።
በዚህም በኢትዮጵያ እና በእስራኤል መካከል ያለውን የሁለትዮሽ ግንኙነት የሚያጠናክር ውይይት ማድረጋቸውን አመልክተው፤ በሁለቱ ሀገራት ታሪካዊ እና ባህላዊ ትስስር ላይ ትኩረት በማድረግ መምከራቸውን ጠቁመዋል።
የቤተ-እስራኤል ማህበረሰብ የሀገራቱን ህዝብ የሚያገናኝ ህያው ድልድይ እንደሆነ በማንሳት፤ ይህም በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ጥልቅ ግንኙነት የሚያጎላ እንደሆነ አመልክተዋል።

