Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

የበጎ ፈቃድ አገልግሎት አብሮነትና ማህበራዊ ትስስርን ያጠናክራል – ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 11፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ከልማት ባለፈ አብሮነትንና ማህበራዊ ትስስርን ለማጠናከር ጉልህ ሚና አለው አሉ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)‎ በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ዞን ጎሮ ወረዳ የዘንድሮውን የክረምት የበጎ ፈቃድ ዘመቻ በዛሬው ዕለት በይፋ አስጀምረዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት÷ የሚሰራ እጅ፣ የሚናገር አፍ፣ የሚያስብ አእምሮ ሲሰናሰሉ ነው ልማት እና ለውጥ የሚመጣው።

የክረምት በጎ ፈቃድ ሥራዎቻችን ከበጀት እና ከልማት በላይ ናቸው ፤ በመልካምነት ቁም ነገር ሰርተን እንድናልፍ የሚያስችሉ ናቸው ሲሉም አስገንዝበዋል፡፡

ወጣቶች የክረምት በጎ ፈቃድ ሥራዎችን እንደ ታላቅ የክብር ሥራ መውሰድ እንዳለባቸው ጠቁመው÷ አዛውንቶች ደግሞ በዚያ ውስጥ ባህልንና ቋንቋን ማስተማር አለባቸው ነው ያሉት፡፡

ከሥራ ውጪ የሚገነባ ሀገር እንደሌለና ተባብሮ መስራት ከተቻለ በታሰበው መንገድ የኢትዮጵያን ብልጽግና ማረጋገጥ እንደሚቻል አስረድተዋል፡፡

ቀጣዩ ጊዜ ብዙ ሥራ፣ ብዙ ድካም ያለበት እና ብዙ ውጤት የሚጠበቅበት ዘመን መሆኑን አመልክተዋል፡፡

ከፊታችን ያለው ዘመን መሰረታዊ የሚባል የኢትዮጵያ ችግር መልክ የሚይዝበት ጊዜ ነው ሲሉም አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡

በወንድማገኝ ጸጋዬ

Exit mobile version