Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

የሰውሰራሽ አስተውሎት ሊያስከትል የሚችለውን አደጋ ለማስቀረት በህግ መመራት አለበት – አንቶኒዮ ጉተሬዝ

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 29፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የሰውሰራሽ አስተውሎት በተለይም በህጻናት ላይ ሊያስከትል የሚችለውን አሉታዊ ተጽዕኖ ለማስቀረት በህግ መመራት አለበት አሉ የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸኃፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ፡፡

ዋና ጸኃፊው ይህን ያሉት በሰውሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂ ዙሪያ በመንግሥታት ደረጃ ለመጀመሪያ ጊዜ በጄኔቫ በተካሄደው ዓለም አቀፍ መድረክ ላይ ነው፡፡

ቴክኖሎጂው የዓለምን ኢኮኖሚ፣ ምርጫ፣ የስራ እድል እንዲሁም የጸጥታና ደህንነት ሁኔታ የመወሰን አቅም እንዳለው ገልጸው፥ ነገር ግን ቴክኖሎጂውን የሚጠቀሙ ሰዎች ጭምር ሊቆጣጠሩት በማይችሉት ፍጥነት እያደገ ነው ሲሉ ስጋታቸውን አጋርተዋል፡፡

የሰውሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂ የሚያበረክተው አዎንታዊ አስተዋጽኦ ይበልጥ እንዲጠናከርና በተለይም በህጻናት ላይ ሊያስከትል የሚችለውን አደጋ ለማስቀረት የሚመራበት ዓለም አቀፍ ህግ ተግባራዊ መሆን እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡

መድረኩ የሰውሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂ የሚያስከትለውን ጉዳት ለማስቀረትና መልካም እድሎቹን በአግባቡ ለመጠቀም የሚያስችሉ ህጎች በሚዘጋጁበት ሁኔታ ላይ እንደሚመክር ሮይተርስ ዘግቧል፡፡

40 አባላት ያሉት የባለሙያዎች ቡድን በቴክኖሎጂው ትግበራ ዙሪያ ባከናወነው ጥናት መሰረት ሳይንሳዊ ግኝቶችን በመድረኩ ላይ ማቅረቡም ነው የተገለጸው፡፡

Exit mobile version