Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

ፕሬዚዳንት ሣኅለወርቅ ማህበረሰቡ የዓይን ብሌኑን በመለገስ ለወገኖቹ ብርሃን እንዲሆን ጥሪ አቀረቡ

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 21፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ፕሬዚዳንት ሣኅለወርቅ ዘውዴ ዜጎች ከህልፈት በኋላ የዓይን ብሌናቸውን በመለገስ ለሌሎች ወገኖቹ ብርሃን እንዲሆን ጥሪ አቀረቡ፡፡

ፕሬዚዳንቷ የኢትዮጵያ ዓይን ባንክ የተመሰረተበት 20ኛ ዓመት አከባበር ላይ እንደገለጹት÷ ማህበረሰቡ ስለ ዓይን ልገሳ ያለውን ግንዛቤ የማሳደግ ስራ ማከናወን ይገባል፡፡

ከህልፈት በኃላ በሚደረገው ልገሳ ምንም የምናጣው ነገር አይኖርም ያሉት ፕሬዘዳንቷ÷ ብርሃንን የመሰለ ታላቅ ስጦታ ትኩረት ሊነፈገው አይገባም ብለዋል፡፡

ስለሆነም ዜጎች ከህልፈት በኋላ የዓይን ብሌናቸውን በመለገስ ለሌሎች ወገኖቻቸው ብርሃን እንዲሆኑ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

የጤና ሚኒስትር ዶክተር ሊያ ታደሰ በበኩላቸው÷ የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ የበርካታ ሰዎችን ህይወት የለወጠ ተቋም ነው ሲሉ አውስተዋል፡፡

እስካሁን የዓይን ባንኩ ባደረገው እንቅስቃሴ ከ3 ሺህ ለሚበልጡ ወገኖች ብርሃናቸውን መመለስ መቻሉን የጤና ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል፡፡

Exit mobile version