ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ የታለመለትን ግብ አሳክቷል – ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)
አዲስ አበባ፣ ታሕሣሥ 11፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ የታለመለትን ግብ አሳክቶ ተጠናቋል አሉ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዛሬው እለት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በይፋ አስጀምረዋል፡፡
ተደራሽነትን ማስፋት፣ ለዜጎች እኩል እድል መፍጠር እንዲሁም በዜጎችና ተቋማት መካከል መተማመንን ማጎልበት ደግሞ የስትራቴጂው ቁልፍ መሰረታዊ ትልሞች መሆናቸው አመልክተዋል፡፡
እነዚህ ትልሞች እንዲሳኩ በተለይ የህዝብ ዲጂታል መሠረተ ልማትን ማስፋት ላይ ትልቅ ስራ እንደሚከናወን ገልጸው፥ ይህም ዲጂታል ቴክኖሎጂ ሰው ተኮር ሆኖ የዜጎችን ኑሮ እንዲያሻሽል ትልቅ አቅም ይፈጥራል ነው ያሉት።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ የትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፥ በአጠቃላይ በዲጂታል ኢትዮጵያ የሚከናወኑ ስራዎች የመደመር መንግስት በቀለለ ቢሮክራሲ ታላላቅ ስትራቴጂዎችን እውን ለማድረግ ከያዘው ግብ ጋር የተሳሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል።