የጣሊያን የውጭ ጉዳይና ዓለም አቀፍ ትብብር ምክትል ሚኒስትር የመዲናዋን የወንዝ ዳርቻ ልማት ጎበኙ
አዲስ አበባ፣ መጋቢት 16፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የጣሊያን የውጭ ጉዳይና ዓለም አቀፍ ትብብር ምክትል ሚኒስትር ማሪያ ትሪፖዲ በአዲስ አበባ ከእንጦጦ እስከ አራዳ ያለውን የወንዝ ዳርቻ ልማት እና የአካባቢ ጥበቃ ስራዎችን ጎብኝተዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ በአዲስ አበባ የመጀመሪያው የኢትዮ-ጣሊያን የኮንስትራክሽን ፣ የመሰረተ ልማትና የከተማ መልሶ ማልማት ፎረም እየተካሄደ መሆኑን ገልጸዋል።
ከፎረሙ ጎን ለጎን፣ ከጣሊያን የውጭ ጉዳይና ዓለም አቀፍ ትብብር ምክትል ሚኒስትር ማሪያ ትሪፖዲ ጋር በመሆን ከእንጦጦ እስከ አራዳ ያለውን የወንዝ ዳርቻ ልማትና የአካባቢ ጥበቃ ስራዎችን ጎብኝተናል ብለዋል።
ማሪያ ትሪፖዲ በበኩላቸው የአመራር ጥበብ የታየበት የአዲስ አበባ ወንዝ ዳርቻ ልማት የከተማዋን ደረጃ የሚያሳድግ ነው ሲሉ ገልጸዋል።
በከተማዋ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ሁሉ አስደንቀውኛል ያሉት ምክትል ሚኒስትሯ፤ የወንዝ ዳርቻ ልማቱ ነዋሪውን ታሳቢ አድርጎ መሰራቱ ለሌሎች አረዓያነት ያለው መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ፕሮጀክቱ የሚመራበትን መንገድ እና አሰራር አድንቀው፤ በከተማ ማደስ ስራው ውስጥ ሀገራቸው በትብብር የመስራት ፍላጎት እንዳላት ጠቁመዋል።