Fana: At a Speed of Life!

የመንግስት የምህረትና ይቅርታ እርምጃ፤ ለብሔራዊ የምክክር መድረክ ስኬት መሰረታዊ ጉዳይ ነው – የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 29፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ለአንድ ሀገር እድገትና ብልጽግና ሀገራዊ መግባባት መሰረታዊ ጉዳይ ነው ሲል የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ገለጸ፡፡
 
ክልሉ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ማምሻውን መግለጫ አውጥቷል፡፡
 
የመግለጫው ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል፡-
 
የመንግስት የምህረትና ይቅርታ እርምጃ፤ለብሔራዊ የምክክር መድረክ ስኬት
 
ለአንድ ሀገር እድገትና ብልጽግና ሀገራዊ መግባባት መሰረታዊ ጉዳይ ነው፡፡ በሁሉም ጉዳይ ላይ መግባባት ባይቻል እንኳ፤ብሔራዊ ጥቅማችንና ሉአላዊነታችንን ከውስጥና ውጭ ሃይሎች ከሚጋረጡበት ተግዳሮቶች ለመታደግ፤ እንዲሁም የዜጎች ክብር የሚረጋገጥበትን ጠንካራ ምጣኔ ሀብት በመገንባት ብልጽግናን ለማረጋገጥ ሲባል በመሰራታዊ ሀጋራዊ አጀንዳዎች ዙሪያ መግባባትን መፍጠር ግድ ይላል፡፡
 
በመደመር እሳቤ መዳረሻችንን ብልዕግና አድርገን ጉዞ ስንጀምር ካለፉት ታሪካችን የሚጠቅሙ እና ለቀጣይ ጉዟችን ወረት ሰንቀን የክፋትና የጥላቻ ፋይሎችን በይቅርታና ምህረት ዘግተን ለሁላችን ምቹ የሚሆነውን አዲስ ምእራፍ እንፈጥራለን በሚል ቆራጥ አቋም ይዘን ነበር፡፡
 
በፍቅር እንደመር በይቅርታ እንሻገር የሚለውን ሀገራዊ ጥሪ ተቀብለው መዳረሻቸውን ብልጽግና ያደረጉ በርካታ ተጓዦች ቢኖሩም፤ በቆሞ ቀር የፖለቲካ አሰተሳሰብ በነበሩበት ተቸንከረው የቀሩ አሉ፡፡ እንደ ህወሓትና ሸኔ ይቅርታን ሰጥቶ መቀበል ይቅርና ከነ አካቴው ወደለየለት የአሸባሪነት ድርጊት በመሸጋገር ታሪክ ይቅር የማይላቸውን ግፍና መከራ በዜጎቻችን ላይ ሲፈፅሙ ቆይተዋል፡፡
 
በተለይም አሸባሪው ህወሓት ለእኩይ ተግባሩ ማሰፈጸሚያ ድጋፍ ለማሰባሰብ ሲል ከብልጽግና መሰረታዊ ተፈጥሮና እሳቤዎች ጋር ተቃርኖ የሆኑ አጀንዳዎችን ሆን ብሎ በመዘርጋት ሲያሽጎደጉድ በነበረው ስም የማጥፋት ፕሮፓጋንዳ ትቂት ግለሰቦች በተጠመደላቸው የህወሓት የሴራ ፖለቲካ ሊጠለፉ ችለዋል፡፡ እነኚህ ግለሰቦች አውቀውም ይሁን ባለማወቅ በተጠመደላቸው የሴራ ፖለቲካ ውስጥ ሆነው ሀገርን የማፍረስ ወንጀል ውስጥ ሊዘፈቁ ችለዋል፡፡በመሆኑም በፖለቲካ ጨዋታ ህግጋት ውስጥ ቀይ መስመር በመተላለፋቸው ተጠርጥረው በህግ እንዲጠየቁ ተደርጓል፡፡
 
ይህ ጥፋት ቀላል የማይባል ቢሆንም፤መንግስት ለዘላቂ ሀገራዊ ሰላምና አንድነት፤ እንዲሁም ሁል ግዜ የውጪ ሀይሎች በእጃዙር ከሚቀይሱልን የንትርክና የመጠፋፋት መንገድ ወተን ወደ ብሄራዊ ምክክርና መግባባት እንድንሻገር ያስችለን ዘንድ በይቅርታ እንዲለቀቁ ተድርጓል፡፡
 
ጠንካራ ሀገረ መንግስት ለመገንባት በምናደርገው ትግል የይቅርታ በራችን አንዴ ተከፍቶ ሌላ ግዜ ደግሞ በተስፋ መቁረጥ የሚዘጋ አይደለም፡ይልቁኑ ወደ ብልዕግና የሚያሸጋግረንና ሁሌም የሚያራምደን እንቁ የመደመር እሴታችን በመሆኑ፤ መንግስት ይህንን ታሪካዊ የይቅርታና ምህረት እርምጃ ወስዷል፡፡ይህም መንግስታችን በግዚያዊ ፈተናዎች ሳይንበረከክ ዘላቂ ሰላሟ የተረጋገጠ ምቹ ሀገርን ለትውልድ ለማውረስ የሚያስችል መሰረት እየጣለ መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው፡፡
 
ይህንን የመንግስት የይቅርታና ምህረት እርምጃ ልዩ የሚያደርገው ከውስጥና ከውጭ ሀገርን የመበተን እኩይ ሴራ ሰንቀው የዘመቱብንን ሃይሎች በአይበገሬ ክንዳችን ደቁሰን፤ ሌላውን የሀፍረት ካባ አልብሰን ተላላኪውን ደግሞ ቀብረን እንደ ሀገር ዳግማዊ የአድዋን ድል በማጣጣም ላይ በምንገኝበት ምዕራፍ ሁኔታ ላይ መሆኑ ነው፡፡
 
ጠላቶቻችን ያዘጋጁልንን የጥፋት ወጥመድ በማክሸፍ እጅን በአፍ የሚያስከድን ብሔራዊ ጀብድ ሰርተናል፡፡እንደ ጥንት አባቶቹ ለሀገሩ ክብርና ሉአላዊነት ሲል ለህይወቱ ሳይሳሳ ታሪክ የሚደግም ተውልድ ዛሬም እንዳለ ከታሪክ የማይማሩትን ጭምር አስተምረን ለወዳጅ ኩራት ሆነናል፡፡አሁን ለሌላ ጀግንነትና ድል መንገድ ጀምረናል፡፡ይህ አዲስ የድልና ጀግንነት ጎዳና ለግጭትና አለመግባባት ምክንያት የሆኑትን ችግሮች በብሄራዊ ምክክር ከነሰንኮፉ ነቅለን ወደ ዘላቂ ሰላምና ብሄራዊ መግባባት የሚወስደንን አዲስ ምዕራፍ ለመጀመር መወሰናችን ነው፡፡
 
ቀደም ሲልም ችግሮቻችንን ሁሉ በብሄራዊ ምክክር እንፈታልን ብለን ለመረጠን ህዝብ ቃል መግባታችን ይታወሳል፡፡ምንም እንኳ ዛሬ ከማረሚያ የተለቀቁ ግለሰቦች ጥፋተኛ ቢሆኑም፤ በምህረት እንዲለቁቁ መደረጋቸው ለሀገራዊ ምክክርና መግባባት እንደቃላችን ሆነን መንገድ መጀመራችንን ያሳያል፡፡
 
በዚሁ ሂደት ከማረሚያ ቤት በምህረት የተለቀቁ ግለሰቦችም ካለፈው ስህተታቸው በመማር የተሰጣቸውን እድል በታለቅ ሃላፊነት እንደሚጠቀሙ መንግስት ተስፋ ያደርጋል፡፡ለተወጠነው ብሄራዊ ምክክር ዓላማም ህጋዊ መሰረትን በጠበቀ መልኩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚደረጉ ያምናል፡፡
 
በምክክር ችግሮቻችንን እንፈታልን፤ጀምረናል፤በዘላቂነት እናሳካዋልን፡ዛላቂ ሰላምና፤ ሁለንተናዊ ብልጽግናን እናረጋግጣልን!
 
የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት
 
ታህሳስ 29፣ 2014
 
ፊንፊኔ
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.