የደቡብ ኮሪያ፣ የጃፓን እና አሜሪካ የጦር ባለሥልጣናት በቀጠናዊ የፀጥታ ጉዳይ ላይ ሊመክሩ ነው
አዲስ አበባ ፣ መጋቢት 20 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የደቡብ ኮሪያ ጦር አዛዥ ዎን ኢንቾል እንዲሁም የአሜሪካ እና የጃፓን አቻዎቻቸው ማርክ ሚሊ እና ኮጂ ያማዛኪ በነገው ዕለት በቀጠናዊ የደኅንነት ጉዳዮች ላይ እንደሚመክሩ ተገለጸ፡፡
የጦር አዛዦቹ በሃዋይ ተገናኝተው እንደሚመክሩ ሲ ጂ ቲ ኤን በዘገባው አመላክቷል።
በውይይታቸው የኮሪያን ባሕረ – ሠላጤ እና የሰሜን ምሥራቃዊ እስያ ቀጠናዎችን ደኅንነት እና ፀጥታ በትብብር ማረጋገጥ በሚቻልበት ጉዳይ ላይ ይመክራሉ ተብሏል።
ዘ ኮሪያ ሄራልድ በዘገባው እንዳመላከተው የሀገራቱ የጦር ባለሥልጣናት በጉዳዩ ላይ ለመነጋገር የቀጠሩት ባሳለፍነው ሐሙስ ሰሜን ኮሪያ አኅጉር አቋራጭ የባላስቲክ ሚሳኤል ሙከራ ማድረጓን ተከትሎ በተፈጠረባቸው ሥጋት ነው፡፡
ይህ የሰሜን ኮሪያ የሚሳኤል ሙከራ በዚህ ዓመት ብቻ ለ 12ኛ ጊዜ የተደረገ ነው ተብሏል፡፡
ሰሜን ኮሪያ በዚህ ዓመት ጥር ወር ብቻ ሰባት አኅጉር አቋራጭ የሚሳኤል ሙከራ ማድረጓም ነው የተጠቆመው፡፡