Fana: At a Speed of Life!

የአማራ ክልል ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ 153 ቢሊየን ብር ካፒታል ላስመዘገቡ ባለሀብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ ሰጠ

አዲስ አበባ ፣ ሐምሌ 30 ፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የአማራ ክልል ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ 153 ቢሊየን ብር ካፒታል ላስመዘገቡ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፍቃድ መስጠቱን አስታወቀ።

የክልሉ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ይኸነው ዓለም ÷ በ2012 በጀት ዓመት ለ2 ሺህ 214 ባለሀብቶች ፍቃድ ለመስጠት ታቅዶ ለ2 ሺህ 908 ባለሀብቶች ፍቃድ መሠጠቱን ተናግረዋል።

የኢንቨስትመንት ፍቃድ ከወሰዱት ባለሀብቶች ውስጥ 291 የሚሆኑት ወደ ስራ የገቡ መሆናቸውንም ነው የገለጹት ።

ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸርም 74 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱን ዳይሬክተሩ አስረድተዋል።

አቶ ይኸነው ዓለም አያይዘውም 47 ነጥብ 99 ቢሊየን ብር ካፒታል ላስመዘገቡ ባላሃብቶች ፍቃድ ለመስጠት ታቀዶ ÷153 ቢሊየን ብር ካፒታል ላስመዘገቡ ባለሀብቶች ፍቃድ መሰጠቱን አስረድተዋል ።

ከስራ እድል አኳያም ለ228 ሺህ 42 ዜጎች የስራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ ÷ ለ 395 ሺህ 804 ዜጎች የስራ ዕድል ይፈጥራሉ ብለዋል ።

ለክልሉ ኢንቨስትመንት መጨመር÷ የክልሉ ሰላምና ደህንነት ካለፉት አመታት የተሻለ መሆን፣ የህብረተሰቡ የመልማት ጥያቄ፣ የክልሉ ተወላጅ ባለሀብቶች የማልማት ፍላጎት ማደግ እንዲሁም የአመራሩ ቁርጠኝነት ዋና ዋና ምክንያቶች መሆናቸውን ዳይሬክተሩ አንስተዋል።

በናትናኤል ጥጋብ

#FBC
የዜና ሰዓት ሳይጠብቁ የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬትን ትኩስ እና ሰበር ዜናዎችን በፍጥነት በአጭር የፅሁፍ መልዕክት መልክ በስልክዎ ላይ እንዲደርስዎ ወደ 8111 OK ብለው ይላኩ።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.