Fana: At a Speed of Life!

በመዲናዋ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የዳግም ምዝገባ መረጃ እስከ ሰኔ 30 ይፋ ይሆናል

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 17፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በአዲስ አበባ የሚገኙ 73 የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የዳግም ምዝገባ መረጃ እስከ ሰኔ 30 ቀን 2017 ዓ.ም ይፋ ይሆናል አለ የትምህርትና ስልጠና ባለስልጣን።

የባለስልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ቢኒያም ኤሮ ለፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን እንደገለጹት÷ በሀገሪቱ የሚገኙ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የዳግም ምዝገባ እየተካሄደ ይገኛል።

ከ375 የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ 85ቱ አስፈላጊውን መስፈርት ባለማሟላት ከትምህርት ሥርዓት ራሳቸውን በማግለል ተማሪዎቻቸውንና የተማሪዎችን ማስረጃ ስራ ላይ ለሚገኙ ተቋማት እያስተላለፉ ነው ብለዋል።

አብዛኛዎቹ የግል ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትም ከህንጻ፣ ከመምህራን ሁኔታ፣ ከአጠቃላይ የትምህርት መሰረተ ልማት እና ከሰው ኃይል አንጻር ከፍተኛ ክፍተት እንዳለባቸው አንስተዋል።

ባለስልጣኑ ያወጣውን መስፈርት የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሙሉ በሙሉ እንደማያሟሉ ገልጸው÷ ተቋማቱን እየደገፍንና እያበቃን እንሄዳለን ነው ያሉት።

መንግስት የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ከትምህርት ሥርዓቱ የማስወጣት ፍላጎት እንደሌለው እና በማብቃት እውቅና እንዲያገኙ እንደሚሰራ እንዲሁም ከስራው የወጡት መስፈርቱን ሲያሟሉ በድጋሚ መመለስ እንደሚችሉ አስረድተዋል።

ተቋማቱ 50 በመቶ የዳግም ምዝገባ መስፈርቶችን ማሟላት እንደሚጠበቅባቸው አስታውሰው÷ አሁን ላይ በመዲናዋ የሚገኙ 73 የግል ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የዳግም ምዝገባ መረጃ እስከተያዘው ወር መጨረሻ ድረስ ይፋ እንደሚሆንም ነው የተናገሩት።

በዳግም ምዝገባው የሚቀጥሉና የማይቀጥሉ ተቋማት መረጃ ለህዝብ ይፋ እንደሚደረግ እና በክልሎች የተጀመረው የዳግም ምዝገባ ስራም በአጭር ጊዜ ውስጥ ይፋ እንደሚደረግ ጠቁመዋል፡፡

በመሳፍንት እያዩ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.