Fana: At a Speed of Life!

በኦሮሚያ ክልል የወተት ምርት ገበያ ትስስርን ለማሳለጥ…

አዲስ አበባ፣ ሕዳር 4፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በኦሮሚያ ክልል በ2018 በጀት ዓመት ባለፉት 3 ወራት 1 ነጥብ 5 ቢሊየን ሊትር ወተት ተመርቷል አለ የክልሉ ግብርና ቢሮ፡፡

የቢሮው ም/ሃላፊና የእንስሳት ዘርፍ ሃላፊ አቶ ቶሌራ ደበላ ለፋና ዲጂታል እንዳሉት ÷ በበጀት ዓመቱ የወተት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በልዩ ትኩረት እየተሰራ ነው፡፡

በዚህም መሰረት በዘርፉ የሌማት ትሩፋት እና ሌሎች አዳዲስ ኢኒሼቲቮችን በመተግበር ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ ነው ብለዋል፡፡

የወተት ምርታማነትን ለማሳደግ በመደበኛ የማዳቀል እና ሌሎች መንገዶች የተሻሻሉ የላም ዝርያዎችን ማቅረብ መቻሉን ተናግረዋል፡፡

በበጀት ዓመቱ 4 ነጥብ 8 ቢሊየን ሊትር ወተት ለማምረት መታቀዱን ጠቁመው ÷ በሩብ ዓመቱም 1 ነጥብ 5 ቢሊየን ሊትር ወተት መመረቱን አመልክተዋል፡፡

በክልሉ የወተት ምርት ገበያ ትስስር ላይ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመፍታት ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡

የዘርፉን ገበያ ትስስር ሥርዓት ለማስያዝና ሕገ ወጥ ነጋዴዎችን ለመከላከል ኮሚቴ ተዋቅሮ ልዩ ቁጥጥር እያደረገ ይገኛል ነው ያሉት፡፡

ወተትና የወተት ውጤቶች በፋብሪካ ሒደት አልፈው ወደገበያ እንዲቀርቡ የግንዛቤ ማስጨበጥ ሥራ በሥፋት እየተሰራ መሆኑን አብራርተዋል፡፡

ለዚህም የወተት ምርትን በጥቃቅንና አነስተኛ ወይም ማህበራት የተደራጁ ወጣቶች እንዲሰበስቡና ለፋብሪካዎች እንዲያስረክቡ መመሪያ ወጥቶ እየተተገበረ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በመላኩ ገድፍ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.