Fana: At a Speed of Life!

የትራንስፖርት ታሪፍ በተወሰነው መሰረት እንዲቀጥል ትዕዛዝ ተላለፈ

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 21፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር የትራንስፖርት ታሪፍ በተወሰነው መሰረት ብቻ እንዲቀጥል ተዕዛዝ አስተላልፏል።

ሚኒስቴሩ የትራንስፖርት አገልግሎት ወደ መደበኛ ሁኔታ መመለሱን ለማሳወቅ ባወጣው መግለጫ÷ በመካከለኛው ምሥራቅ የተከሰተው ግጭት በዓለም አቀፍ የነዳጅ ገበያ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ አሳድሮ የነዳጅ ዋጋ ግሽበትና በአቅርቦት ላይ መስተጓጎል እንዲፈጠር አድርጓል ብሏል።

ይህም ሁኔታ በኢትዮጵያ የናፍታ ዕለታዊ አቅርቦትን ከ9 ሚሊየን ሊትር ወደ 4 ነጥብ 5 ሚሊየን ሊትር እንዲቀንስ አድርጎ በትራንስፖርት አገልግሎት ላይ የሚታወቁ መስተጓጎሎችን አስከትሎ እንደነበር አስታውሷል።

መንግሥት ይህንን ችግር በፍጥነት ለመቆጣጠር የታሪፍ ማሻሻያ፣ የአቅርቦት አደረጃጀት ማሻሻል እና የሎጂስቲክስ ቅንጅት ማጠናከርን ጨምሮ በርካታ አስቸኳይ እና ዘላቂ ርምጃዎች መውሰዱን አመልክቷል።

ይህም የውጭ ጫናዎች ቢኖሩም የሀገር ውስጥ ኢኮኖሚ መረጋጋትን በመጠበቅ እና የሕዝብ አገልግሎቶች እንዳይቋረጡ በማድረግ በኩል መንግሥት የሕዝብ ጥቅምን በማስቀደም የሚከተለውን የፖሊሲ አቅጣጫ የሚያሳይ መሆኑን አስረድቷል።

ዛሬ የገንዘብ ሚኒስቴር በይፋ እንዳሳወቀው የነዳጅ አቅርቦት ወደ መደበኛ ሁኔታው ተመልሷል ያለው ሚኒስቴሩ÷ ይህ ሁኔታ በትራንስፖርት ዘርፍ የተፈጠሩ መስተጓጎሎች በፍጥነት እንዲፈቱ ያስችላልም ብሏል።

በመሆኑም ከዛሬ ጀምሮ ቀደም ሲል በነዳጅ እጥረት ምክንያት የተፈጠሩ የትራንስፖርት አገልግሎት መስተጓጎሎች ሙሉ በሙሉ እንዲቀረፉ፣ ከአዲስ አበባ እስከ ክልሎች የሚገኙ ሁሉም የዘርፉ አመራሮች እና ተዋናዮች ታሪፍ በተወሰነው መሰረት ብቻ እንዲቀጥል በጥብቅ እንድከታተሉና ትግበራውንም በጋራ ግብረ ኃይል እንዲያረጋግጡ አሳስቧል፡፡

መንግሥት የሕዝብ ኑሮ መረጋጋትን ማረጋገጥ፣ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ቀጣይነትን መጠበቅ እና የትራንስፖርት አገልግሎት በዘላቂ መልኩ እንዲጠናከር ያለውን ቁርጠኝነት ይቀጥላል ሲልም አስገንዝቧል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.