በ2018 በጀት ዓመት ከወጪ ንግድ 607 ሚሊየን ዶላር ገቢ ተገኘ
አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 22፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በ2018 በጀት ዓመት ከአምራች ዘርፉ ወደ ውጭ ከተላኩ ምርቶች 607 ሚሊየን ዶላር ገቢ ተገኝቷል አለ የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር።
ሚኒስቴሩ በአምራች ዘርፉ የተሻለ የወጪ ንግድ አፈጻጸም ካሳዩ አምራቾች ጋር እየተወያየ ነው፡፡
የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል በዚህ ወቅት እንዳሉት÷ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ከጀመረ በኃላ ከውጭ የሚገባን ምርት በሀገር ውስጥ የመተካትና የውጭ ምንዛሬ እድገት አሳይቷል፡፡
በዚህም የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ከመጀመሩ በፊት 385 ሚሊየን ዶላር የነበረው የውጭ ምንዛሬ ግኝት አሁን ላይ በዓመት 607 ሚሊየን ዶላር መድረሱን ገልጸዋል፡፡
መንግስት ለአምራች ዘርፉ በሰጠው ትኩረት ዘርፉ መሰረታዊ ለውጦችን እያስመዘገበ ነው ብለዋል፡፡
በቀጣይ በጀት ዓመት በአምራች ዘርፉ ወደ ውጭ ከሚላከው ምርት 1 ቢሊየን ዶላር ገቢ ለማግኘት መታቀዱንም አመልክተዋል።
በዓመት ከ162 ሺህ የማይበልጥ የነበረው በአምራች ዘርፉ የሚፈጠረው የስራ እድል አሁን ላይ ከ433 ሺህ በላይ መድረሱን አብራርተዋል፡፡
በአምራች ዘርፉ ወደ ውጭ የሚላከውን ምርት ለማሳደግና የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ለማሻሻል የወጪ ንግድ ስትራቴጂ መዘጋጀቱን ሚኒስትሩ ጠቁመዋል፡፡