ማዕዘናትን ማገናኘት
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 1፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማ ተሸካሚው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ ጋር የሚጣጣም የሀገር ውስጥ የበረራ መረቡን በማስፋት መዳረሻዎቹን ማሳደጉን ቀጥሏል።
በአውሮፕላን ማረፊያ መሰረተ-ልማቶች፣ በአውሮፕላኖች ግዥ እና በአዳዲስ የበረራ መስመሮች ላይ በሚደረግ
ኢንቨስትመንት አየር መንገዱ የኢኮኖሚ ቅንጅትን በማፋጠን፣ ሀገራዊ አንድነትን በማጠናከር እና ሁሉንም የሀገሪቱ ማዕዘናት የልማቱ ተቋዳሽ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል።
ባለፉት ጥቂት ዓመታት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቀደም ሲል ለመድረስ አስቸጋሪ የነበሩ አካባቢዎችን በቀጥታ ከሀገሪቱ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ጋር ለማገናኘት የሀገር ውስጥ ተደራሽነቱን አስፍቷል።
በዚህ የሀገር ውስጥ ማስፋፊያ ከተካተቱት መካከል ነጌሌ ቦረና፣ ጎሬ መቱ፣ ደብረ ማርቆስ እና ያቤሎን የመሳሰሉ አዳዲስ የተገነቡና የተሻሻሉ የአውሮፕላን ማረፊያዎችን ማካተቱ የአየር መንገዱን የሀገር ውስጥ የበረራ መረብ ወደ 26 መዳረሻዎች ከፍ አድርጎታል።
የመዳረሻዎች መስፋፋት መዲናዋን ከብዙዎቹ የሀገሪቱ አካባቢዎች ጋር ያላትን ትራንስፖርት ትስስርን ያጠናከረ ሲሆን፤ ቀናት ይወስዱ የነበሩ የትራንስፖርት አገልግሎቶችን በሰዓት ውስጥ እንዲሰጥ አስችሏል።
ይህ የታለመ ስትራቴጂ በመደበኛ መጓጓዣ ያልተዳረሱ የኢኮ-ቱሪዝም ቦታዎች እና ከፍተኛ ቅድመ-አስፈላጊነት ላላቸው የክልል ኢንቨስትመንት ቀጠናዎች መዳረሻን ይከፍታል።
የክልል መዳረሻዎች ወሳኝ የሆኑ የግብርና ማዕከላት እንደመሆናቸው የቀጥታ በረራ ትስስር ከፍተኛ ዋጋ ያላቸው ምርቶች በፍጥነት ወደ ሀገር ውስጥ እና ወደ ውጭ ንግድ መስመሮች እንዲደርሱ ያስችላል።
የተሻሻለው የሀገር ውስጥ የበረራ ድግግሞሽ የውጭ ሀገር ጎብኚዎችንም ሆነ የሀገር ውስጥ ቱሪስቶችን የሀገሪቱን የተለያዩ ባህላዊ ሀብቶች፣ ቅርሶች እንዲሁም የቱሪስት መዳረሻ የኢኮ-ቱሪዝም መስህቦች እንዲጎበኙ ያበረታታል።
ከንግድ ባሻገር፣ የተስፋፋው የክልል የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት የህክምና ድንገተኛ ጉዞዎች በከፍተኛ ሁኔታ እንዲሻሻሉ ወሳኝ የመድኃኒት አቅርቦቶች እና ድንገተኛ ሰብአዊ ርዳታዎች በፍጥነት እንዲሰራጩ ያግዛል።
እንደ ጂንካ፣ ጎዴ እና ባሌ ሮቤ ባሉ የክልል አውሮፕላን ማረፊያዎች የመንገደኞች ተርሚናሎች ላይ የተደረገው ማሻሻያ እንዲሁም ትናንት የተመረቀው የባህር ዳር በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አዲሱ ተርሚናል የክልሎች የአየር ትራንስፖርት አገልግሎትን ያዘምናል፡፡
አካታች እና አስተማማኝ የአየር ትራንስፖርት መረብ መገንባት ሀገራዊ ብልፅግናን ለማረጋገጥ ማዕከላዊ ሚና ያለው በመሆኑ የሀገር ውስጥ በረራን በማዘመን የበረራ መስመሮችን ወደ እያንዳንዱ የሀገሪቱ ክልል ማስፋፋት በትኩረት እየተሰራበት ነው፡፡
የፌዴራል መንግሥቱን ሰፊ የመሰረተ-ልማት ማዘመን ጥረቶች አካል የሆነው የሀገር ውስጥ የበረራ መረብ መስፋፋት ከተሞችን ያገናኛል፣ የስራ እድሎችን ይፈጥራል እንዲሁም እያንዳንዱ ክልል ሀገሪቱ ወደ ዘላቂ የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን በምታደርገው ጉዞ እኩል ተጠቃሚ መሆንን ያረጋግጣል።
በዓመት ከ110 ሚሊየን በላይ መንገደኞችን ለማስተናገድ የተነደፈው የ12 ቢሊየን ዶላሩ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክት ግንባታ ሲጠናቀቅ ለአፍሪካ ትልቁ ዓለም አቀፍ የአቪዬሽን በር እና ቀልጣፋ የሀገራቱ ማገናኛ ሆኖ እንደሚያገለግል ይጠበቃል፡፡
በምሕረት ደምሴ