Fana: At a Speed of Life!

በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ ከ2 ሺህ 600 በላይ ካርቶን ዘይት ተከማችቶ ተገኘ

አዲስ አበባ፣ የካቲት 29፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ በማህበረሰቡ ጥቆማ በ8 ነጋዴዎች ላይ በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻና ቁጥጥር ሥራ ከ2 ሺህ 600 በላይ ካርቶን የምግብ ዘይት በህንፃ ምድር ቤት ውስጥ ተከማችቶ መገኘቱን የአዲስ አበባ ፖሊስ ገለፀ።

 

የካቲት 28 እና 29 ቀን 2014 ዓ.ም በክፍለ ከተማው ወረዳ 1 ልዩ ቦታው ሲዳሞ ተራ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በአንድ ህንፃ ምድር ቤት ውስጥ በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ ነው የምግብ ዘይቶቹ ተከማችተው የተገኙት።

ግለሰቦቹ የተሰጣቸውን የንግድ ፈቃድ ሽፋን በማድረግና አሁን ያለውን የዘይት አቅርቦት እጥረት ችግር እንደመልካም አጋጣሚ በመጠቀም አከማችተው እንደተገኙ ተገልጿል፡፡

ከህብረተሰቡ በደረሰ ጥቆማ መሰረት በ8 ነጋዴዎች ላይ በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ ባለ 3 ሊትር 441 ካርቶን፣ ባለ 5 ሊትር 129 ካርቶን፣ ባለ 1 ሊትር 65 ካርቶን፣ ባለ 5 እና 3 ሊትር 2 ሺህ 100 ካርቶን በአጠቃላይ ከ2 ሺህ 600 በላይ ካርቶን የምግብ ዘይት ሊያዝ ችሏል፡፡

ይህም ለህብረተሰቡ በወቅቱ መድረስ የነበረበት ቢሆንም ነጋዴዎቹ በአንድ ህንፃ ምድር ቤት ውስጥ አከማችተው የተገኙ በመሆናቸው መጋዝኖቹም እንዲታሸጉ መደረጉን ከአዲስ አበባ ፖሊስ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

መንግስት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየናረ የመጣውን የኑሮ ውድነት ለመቀነስ የተለያዩ የመፍትሄ እርምጃዎችን እየወሰደ ባለበት ወቅት÷ አንዳንድ ነጋዴዎች ህጋዊ የንግድ ፈቃድን እንደ ሽፋን በመጠቀም ህገ-ወጥ ድርጊት የሚፈጽሙ በመኖራቸው ህብረተሰቡ ከፀጥታ ሀይሉ ጋር በመቀናጀት ጥቆማ ከመስጠት ጀምሮ የተለመደ ትብብሩን አጠናክሮ እንዲቀጥል የአዲስ አበባ ፖሊስ ጥሪውን አቅርቧል።

በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 ልዩ ስሙ ሸራ ተራ በህገ-ወጥ መንገድ የተከማቸ 12 ሺህ 944 ሊትር ዘይት ተይዟል፡፡
የህብረተሰቡን ጥቆማ መሰረት በማድረግ በተደረገ ክትትል 12 ሺህ 944 ሊትር ዘይት መያዙን የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 ንግድ ፅህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ሚሊዮን ፈዲኖ ተናግረዋል።
ምርት በመደበቅ ህብረተሰቡ በኑሮ ውድነት እንዲማረር ለማድረግ በሚሰሩ ስግብግብ ነጋዴዎች ላይ የሚደረገው ክትትልና ቁጥጥር ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን የወረዳው አስተዳደር አስታውቋል።
በተመሳሳይ በቡራዩ ከተማ በተካሄደ ድንገተኛ ፍተሻ ከ211ሺህ ሊትር በላይ የምግብ ዘይት ተይዟል፡፡
ኢትዮጵያን፦ እናልማ፣ እንገንባ፣ እንዘጋጅ
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.