“የዝንጀሮ ፈንጣጣ” እስካሁን በኢትዮጵያ አልተከሰተም- ጤና ሚኒስቴር
አዲስ አበባ፣ ሰኔ26፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) “የዝንጀሮ ፈንጣጣ” በሚባል የሚታወቀው ተላላፊ በሽታ እስካሁን በኢትዮጵያ አለመከሰቱን ጤና ሚኒስቴር አረጋገጠ፡፡
“የዝንጀሮ ፈንጣጣ” በኢትዮጵያ ተከስቶ ሁለት ሰዎች ተለይተዋል (ኳረንቲን ገብተዋል) የሚል መረጃ በሪፖርተር ጋዜጣ ወጥቶ በማህበራዊ ሚዲያ እየተሰራጨ መሆኑን የጠቀሰው ሚኒስቴሩ÷ በሽታው በሌሎች ሀገራት ቢከሰትም በኢትዮጵያ እስካሁን የተያዘም ሆነ የተለየ ሰው አለመኖሩን አስታውቋል፡፡
ኃላፊነት የሚሰማቸው የሚዲያ ተቋማት ይህን መሰል ያልተረጋገጠና በሚመለከተው አካል ያልቀረበ መረጃን ከማሰራጨት እንዲቆጠቡም ነው ሚኒስቴሩ አሳስቧል፡፡
ወቅታዊ የጤና መረጃዎችን እንዲሁም የማህበረሰቡ የጤና ስጋት የሚሆኑ ወረርሽኞችን በተመለከተ ትክክለኛ መረጃ ከጤና ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ብቻ ማግኘት እንደሚገባም ነው ሚኒስቴሩ ያሳሰበው፡፡
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!