Fana: At a Speed of Life!

ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ  በደባርቅ ከተማና በዳባት ወረዳ 39 ሚሊየን ብር መድቦ በችግር ውስጥ ለሚገኙ ወገኖች ድጋፍ እያደረገ ነው ተባለ

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 11፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ የምዕራብ አማራ ቤቴ ፕሮጀክት በደባርቅ ከተማ አስተዳደርና በዳባት ወረዳ  39 ሚሊየን ብር መድቦ  ለተፈናቃዮች ፣ በችግር ውስጥ ለሚገኙ ወገኖችና ለተቋማት ድጋፍ እያደረገ መሆኑ ተገለጸ።

 

ፕሮግራሙ  ከተለያዩ ቦታዎች ተፈናቅለው በአካባቢው ለሚገኙ ወገኖችና ለችግር ለተጋለጡ ነዋሪዎች የንጽህና መጠበቂያ ቁሳቁስ ፣ የዕለት ደራሽ ምግብና የገንዘብ ድጋፍ  አድርጓል ነው የተባለው፡፡

 

ከ 1ሺህ 100 በላይ ለሚሆኑ ተማሪዎች የገንዘብ ድጋፍ በማድረግና መምህር በመቅጠር የተፋጠነ ስርዓተ ትምህርት በመዘርጋት እያስተማረ መሆኑ ተጠቅሷል።

 

በወርልድ ቪዥን ኢትዮጰያ ምዕራብ አማራ ቤቴ ፕሮጀክት አስተባባሪ ወይዘሮ እየሩሳሌም እያዩ እንዳሉት÷ በሁለቱ አካባቢዎች ለሚገኙ የትምህርት ተቋማት  ወንበሮች ፣ ድንኳኖች እና የቤት ውስጥና ውጭ የልጆች መጫዎቻዎች ድጋፍ ተደርጓል።

 

በቀጣይም  በመጠለያ ጣቢያዎች የሚገኙ ህጻናትና ታዳጊዎች ወደ ትምህርታቸው በሚመለሱበት ሁኔታ ላይ ትኩረት ሰጥተው መስራታቸውን እንደሚቀጥሉ ተናረዋል፡፡

 

የዳባት ወረዳ ትምህርት ጽ/ቤት ሃላፊ አቶ አትርሳው ክንዴ በበኩላቸው÷ ፕሮጀክቱ በወረዳው ለሚገኙ የትምህርት ተቋማት ካደረገው የቁሳቁስ ድጋፍ ባሻገር በችግር ውስጥ ለሚገኙ ተማሪዎች በነፍስ ወከፍ 4ሺህ ብር በመስጠት ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ አስችሏል ብለዋል ።

 

የደባርቅ ከተማ አስተዳደር ሴቶችና ህጻናት መመምሪያ ሃላፊ ወይዘሮ የሽወርቅ  ሞላ በበኩላቸው÷ ፕሮግራሙ በጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችና በስርዓተ ጾታ ላይም የአመለካከት ለውጥ ለማምጣት እየሠራ ያለው ተግባር የሚደነቅ መሆኑን ተናግረዋል።

 

በበላይነህ ዘለዓለም

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.