የሽብር ቡድኑ ህወሓት ታጣቂዎች በሁሉም ግንባር እጅ እየሰጡና እየተበተኑ ነው – መከላከያ ሚኒስቴር
አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 15፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት በወሰደው ከባድና ፈጣን እርምጃ የሕወሓት ታጣቂዎች መበተናቸው እና የታደሉት እጅ መስጠታቸው ተገለፀ፡፡
ሌሎች ደግሞ በተሳሳተ መረጃ ተደናግረው ምን ማድረግ እንዳለባቸው ግራ እንደተጋቡ መረጃዎች እንዳመላከቱ የኢፌዴሪ መከላከያ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ ገልጿል ።
በቅርቡ ለመከላከያ እጅ የሰጡ የአሸባሪው ሕወሓት ታጣቂዎች የክፋት አዝማቾቻቸውን ሁኔታ “ማሽላውን ከአደጋ ለመከላከል የከበበው አጥር ለማሽላው እንጂ ራሱ አጥሩን አልጠቀመውም” ሲሉ እንደገለፁትም ከጦርነቱ ጁንታው እንጂ ታጣቂዎቹ ያተረፉት እልቂት ብቻ መሆኑን ያሳያል ነው ያለው።
በመሆኑም የተበተኑና ከሽብር ቡድኑ የጥፋት ወጥመድ ማምለጥ የሚፈልጉ የአሸባሪው ሕወሓት ታጣቂዎች መከላከያ ወደ ተቆጣጠራቸው የትግራይ አካባቢዎችና ወደ አጎራባች ክልሎች በመሄድ እጃቸውን በሰላም እንዲሰጡም ጥሪ አቅርቧል፡፡
እጃቸውን ለሚሰጡ የሽብር ቡድኑ ታጣቂዎችም አስፈላጊው ክብካቤ እንዲደረግ መመሪያ መተላለፉም ነው ያስታወቀው።
የአጎራባች ክልሎችና ከህወሓት የሽብር ቡድን የተላቀቁ የትግራይ አካባቢዎች ሕዝብ ደግሞ እጅ የሚሰጡ የሽብር ቡድኑ ታጣቂዎችን በመቀበል፣ ተንከባክቦ ለመከላከያ ሠራዊቱ እንዲያስረክብም መልእክት አስተላልፏል፡፡