“በኢትዮጵያ ኢንቨስት ያድርጉ 2023” ፎረም ነገ ይጀመራል
አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 17፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) “በኢትዮጵያ ኢንቨስት ያድርጉ 2023” በሚል መሪ-ቃል የተዘጋጀ ዓለም አቀፍ የኢንቨስትመንት መድረክ በነገው ዕለት በአዲስ አበባ ይከፈታል፡፡
መድረኩን ያዘጋጀው የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ሲሆን ፥ እስከ ሚያዝያ 20 ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ገልጿል፡፡
በመድረኩ ከዓለም ዙሪያ የተውጣጡ ባለሐብቶች ፣ የንግድ አዋቂዎች ፣ፖሊሲ አውጪዎች እና ሥራ ፈጣሪዎች ይሰባሰባሉም ነው የተባለው፡፡
አዲስ ዕይታዎች በኢትዮጵያ ያሉ የኢንቨስትመንት ዕድሎችና ባለሐብቶች መዋዕለ-ንዋያቸውን የሚያፈሱባቸው የሥራ አማራጮች እንደሚቀርቡም ኮሚሽኑ አስታውቋል፡፡
መርሐ-ግብሩ “መዋዕለ-ንዋይዎን በኢትዮጵያ ያፍሱ እና ይደጉ – ኢትዮጵያ ማራኪ የኢንቨስትመንት ዕድሎች ምድር” በሚል መሪ ቃል ይካሄዳል።
በመድረኩ ከ600 በላይ ዓለምአቀፍ ኢንቨስተሮች እንደሚሳተፉበት ተገልጿል፡፡
በሚፈጠሩት የኢንቨስትመንት አማራጮችና ዕድሎች በሚቀጥሉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ ከ3 ቢሊየን ዶላር በላይ የሚሆን መዋዕለ-ንዋያቸውን ይዘው ኢንቨስት ለማድረግ ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡ ባለሐብቶች እንደሚፈጠሩም ኮሚሽኑ በመረጃው ጠቁሟል፡፡