የሱልጣን አሊሚራህ ሐንፍሬ ቤተ መንግስትን ማደስ የአፋርን ታሪክ ማደስ ነው – ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ
አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 21፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የሱልጣን አሊሚራህ ሐንፍሬ ቤተ-መንግስትን ማደስ የአፋርን ታሪክ እንደገና ማደስ ነው ሲሉ የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አወል አርባ ገለጹ።
የመደመር ትውልድ መጽሐፍን የማስተዋወቅ፣ የሽያጭ እና የማስመረቅ መርሐ-ግብር በሰመራ ከተማ ተካሄዷል።
በመርሐ-ግብሩ ላይ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ፣ የክልሉ ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አሲያ ካሚል፣ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
በመርሐ-ግብሩ ከ160 ሚሊየን ብር በላይ መሰብሰቡም ተገልጿል።
ከመጽሐፉ ሽያጭ የሚሰበሰበው ገንዘብ አይሳኢታ ከተማ ለሚገኘው የሱልጣን አሊሚራህ ሐንፍሬ ቤተ-መንግስት እድሳትና ግንባታ የሚውል ነው መባሉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
“የሱልጣን አሊሚራህን ቤተ-መንግስት ማደስ ማለት ታሪክን ማደስ ነው ያሉት” ርዕሰ መስተዳድሩ ስለ ኢትዮጵያ ባንዲራ “እንኳን እኛ ግመሎቻችን የኢትዮጵያን ባንዲራ ያውቁታል” በማለት የተናገሩን ሀሳብ በማንሳት አውስተዋል።
ከመጽሐፋ በሚገኘው ገቢ የሚታደሰው ቤተ-መንግስት ቦታውን ይበልጥ የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ እንደሚያስችልና ሌሎች የቱሪዝም ሀብቶችን ለማልማት በር የሚከፍት መሆኑንም አመልክተዋል።