የቻይናው ኪው ዣ ሲሚንቶ ፋብሪካ በሲሚንቶ አምራችነት መሰማራት እንደሚፈልግ ገለጸ
አዲስ አበባ ፣ ሐምሌ 27 ፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የቻይናው ኪው ዣ ሲሚንቶ ፋብሪካ በድሬዳዋ አስተዳደር በሲሚንቶ አምራችነት መሰማራት እንደሚፈልግ ገለጸ።
የቻይና ባለሃብቶች ልዑካን ቡድን ከድሬዳዋ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች ጋር በመሰረተ ልማትና የአረንጓዴ ልማት ስራዎችን ጨምሮ በአስተዳደሩ ባለው ምቹ የኢንቨስትመንት አማራጮች ዙሪያ ተወያይቷል።
በዚህ ወቅትም የልዑካን ቡድኑ በድሬዳዋ በሲሚንቶ አምራችነት መሰማራት እንደሚፈልጉ መግለጻቸውን የድሬዳዋ አስተዳደር የመንግስት ኮሙኒኬሽን መረጃ ያመላክታል።
ባለሃብቶቹ በግንባታ፣ በአሉሚኒየም፣ በወረቀት፣ በሪልስቴትና ትራንስፖርትን ጨምሮ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች የተሰማሩ ናቸው።
በአስተዳደሩ የአየር ፣ የባቡር፣ የደረቅ ወደብ ፣ የንግድ ቀጠና እንዲሁም ሌሎች ለኢንቨስትመንት ምቹ የሆኑ አማራጮች መኖራቸውን ተከትሎ የውጭ ሀገር ባለሃብቶች በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች የመሰማራት ፍላጎት እንዳላቸው ገልጸዋል።