ፊንላንድ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ትብብር እንደምታጠናክር ገለጸች
አዲስ አበባ፣ ሰኔ 3፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ፊንላንድ ከኢትዮጵያ ጋር በንግድ እና ልማት ዘርፍ ያላትን ትብብር አጠናክራ እንደምትቀጥል ገለጸች፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴዔታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ ከፊንላንድ የውጭ ንግድና ልማት ሚኒስትር ቪሌ ታቪዮ ጋር ተወያይተዋል፡፡
በውይይታቸውም÷በሀገራቱ የሁለትዮሽ ግንኙነት እና ተያያዥ ቀጣናዊ ጉዳዮች ዙሪያ በትኩረት መክረዋል፡፡
አምባሳደር ምስጋኑ÷ፊላንድ በኢትዮጵያ በተለይም በንግድና ኢንቨስትመንት ዘርፍ ንቁ ተሳትፎ እንድታደርግ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ፊንላንድ ለኢትዮጵያ በተለያዩ ዘርፎች ላደረገችው ድጋፍ ምስጋና ማቅረባቸውንም የሚኒስቴሩ መረጃ ያመላክታል፡፡
ቪሌ ታቪዮ በበኩላቸው÷ፊንላንድ ከኢትዮጵያ ጋር በንግድና ልማት ዘርፍ ያላትን ትብብር ይበልጥ እንደምታጠናክር ተናግረዋል፡፡
ሁለቱ ወገኖች በቅርቡ የኢትዮ-ፊላንድ የጋራ የፖለቲካ ምክክር መድረክ ለማካሄድ መስማማታቸውም ተገልጿል፡፡