የኢትዮጵያን ኢንቨስትመንት የሚያስተዋውቅ ፎረም በዶሃ ተካሄደ
አዲስ አበባ፣ ሰኔ 6፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በኢትዮጵያ ያሉ ምቹ የቢዝነስና የኢንቨስትመንት አማራጮችን የሚያስተዋውቅ ፎረም በበይነ መረብ ተካሄደ፡፡
በኳታር፣ ኢራን እና የመን የኢትዮጵያ አምባሳደር ፈይሰል አልይ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር÷ ኢትዮጵያ ለኢንቨስትመንት ምቹ የሆነ ዕምቅ ሀብት ያላት መሆኑን አንስተዋል፡፡
በኳታር እና በኢትዮጵያ መንግስታት መካከል ያለው የኢንቨስትመንት የሁለትዮሽ ትብብር ስምምነት የኳታር ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ባሉ የኢንቨስትመንት አማራጮች እንዲሳተፉ የሚያበረታታ መሆኑን ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን የፕሮሞሽን ባለሙያ አቶ መኮንን ሀይሌ÷ የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች፣ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት የሚስቡ አዳዲስ አሰራሮች እና ማበረታቻዎችን መንግስት ተግባራዊ ማድረጉን አስረድተዋል።
በተጨማሪም ቅድሚያ በተሰጣቸው የኢንቨስትመንት መስኮች ዙሪያ ማብራሪያ መስጠታቸውን ፎረሙን ያዘጋጀው በኳታር የኢትዮጵያ ኤምባሲ መረጃ ያመላክታል፡፡
በኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የመካከለኛው ምስራቅ ኤዥያ እና ፓስፊክ ሀገሮች ጉዳዮች ዳ/ጀኔራል አምባሳደር ገበየሁ ጋንጋ በበኩላቸው÷ የኳታር ኩባንያዎች በኢትዮጵያ ባሉ የኢንቨስትመንት አማራጮች መዋዕለ ንዋይ እንዲያፈሱ ጥሪ አቅርበዋል።