በሶማሌ ክልል በግጦሽ መሬት ላይ ተከሰቶ የነበረው የእሳት አደጋ በቁጥጥር ስር ዋለ
አዲስ አበባ፣ ሰኔ 17፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በሶማሌ ክልል ጀረር ዞን ጋሻሞ ወረዳ በግጦሽ መሬት ላይ ተከስቶ የነበረው የእሳት አደጋ በቁጥጥር ስር መዋሉን የወረዳው አስተዳደር አስታውቋል።
በወረዳው በሚገኝ ሰፊ የግጦሽ መሬት ላይ በትናንትናው ዕለት ቀን 9 ሰዓት ጀምሮ ድንገተኛ የእሳት አደጋ መከሰቱ ተገልጿል፡፡
የእሳት አደጋውን በቁጥጥር ስር ለማዋል ለ7 ሰዓታት በተደረገ ርብርብ ከምሽቱ 3 ሰዓት ላይ መቆጣጠር መቻሉን የክልሉ ኮሙኒኬሽን መረጃ ያመላክታል፡፡
የጋሻሞ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ሙስጠፌ ሂርሲ÷ የእሳት አደጋው በወረዳው በሚገኝ የግጦሽ መሬት ላይ ጉዳት ማድረሱን ተናግረዋል፡፡
የወረዳው ሕዝብ፣ አመራሮችና የፀጥታ አካላት ባደረጉት ርብርብ የእሳት አደጋውን በቁጥጥር ስር ማዋል መቻሉንም አንስተዋል።