በግብፅ እስር ቤቶች የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ እየተስፋፋ መሆኑ ተገለጸ
አዲስ አበባ ፣ ሐምሌ 14 ፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በግብፅ እስር ቤቶች የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ እየተስፋፋ መሆኑን ሂውማን ራይትስ ዎች አስታወቀ።
በዚህም በግብፅ የእስር ማእከላት በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ምክንያት ቢያንስ 14 እስረኞች መሞታቸውን ድርጅቱ ባወጣው ሪፖርት ገልጿል ፡፡
በሀገሪቱ የሚገኙ እስር ቤቶች በቂ ህክምና የሌላቸው ከመሆኑም ባለፈ ቫይረሱን ለመመርመር የሚረዳ ነገር አለመኖሩም ነው የተገለጸው።
የወህኒ ቤቱ ባለስልጣናት ምንም ዓይነት የመከታተያ እርምጃ ያልወሰዱ ከመሆናቸው ባለፈ የቫይረሱን ምልክቶች የሚያሳዩ እስረኞችን ለመለየት እምብዛም አለመስራታቸውን ድርጅቱ ገልጿል።
በተጨማሪም ፖሊሶች ቢያንስ በሶስት እስር ቤቶች ውስጥ ያሉ እስረኞች የፊት ጭምብላቸውን እንዲለብሱ አይፈቅዱም ነው ያለው ፡፡
ከዚያም ባለፈ በግብፅ እስር ቤቶች ውስጥ ስላለው የጤና ሁኔታ መረጃ በባለስልጣናት በጥብቅ ቁጥጥር እንደሚደረግበት ተገልጿል ፡፡
የድርጅቱ ሪፖርት መሰረት ያደረገው የዓይን እማኞች ፣ ከወህኒ ቤቶች በወጡ ደብዳቤዎች እና በሀገር ውስጥ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪ ቡድኖች የወጣን ሪፖርት ነው ተብሏል፡፡
ግብጽ የወረርሽኙን መስፋፋት ለመቀነስ ከየካቲት ወር ጀምሮ 13 ሺህ እስረኞችን ብትለቅም “ ሀገሪቷ ካሏት በእስረኞች የተጨናነቁ እስር ቤቶች አንጻር በሽታውን ለማቃለልና ለማስታገስ በቂ አለመሆኑ ተመልክቷል።
ከዚያም ባለፈ የሀገሪቱ ባለሥልጣናት በእስር ቤቶች “በቂ የሆነ የህክምና አገልግሎት” እንዲኖር እንዲያደርጉ እና ተጨማሪ እስረኞችን እንዲለቁም ድርጅቱ በሪፖርቱ ጠይቋል።
ምንጭ፡-ዴይሊ ኔሽን
#FBC
የዜና ሰዓት ሳይጠብቁ የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬትን ትኩስ እና ሰበር ዜናዎችን በፍጥነት በአጭር የፅሁፍ መልዕክት መልክ በስልክዎ ላይ እንዲደርስዎ ወደ 8111 OK ብለው ይላኩ።