ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኬኛ ቤቨሬጅ ፋብሪካን ጎበኙ
አዲስ አበባ፣ የካቲት 27፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአምቦ ወረዳ በነበራቸው ጉብኝት የኬኛ ቤቨሬጅ ፋብሪካን ተዘዋውረው ተመልክተዋል፡፡
በጉብኝት መርሐ ግበሩ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ እና የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ ተሳትፈዋል፡፡
ፋብሪካው በመጪዎቹ ሶስት ሳምንታት ውስጥ ወደ ሥራ እንደሚገባ የተገለጸ ሲሆን÷ 3 ሚሊየን ሄክቶ ሊትር የማምረት አቅም እንዳለው ተመላክቷል፡፡
የአስተዳደር ሥራን ወደ ሕዝብ ለማቅረብ የቀበሌዎች መጠናከር ወሳኝ መሆኑም ተገልጿል፡፡
ከዚህ ረገድ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት በየአካባቢው ለሕዝብ ቅርብ የሆነ አስተዳደር ለመፍጠር ጥረት እያደረገ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት መረጃ አመልክቷል፡፡
ከዚህ አንጻር በአምቦ ወረዳ የአንድ ቀበሌ እንቅስቃሴ በጉብኝት ወቅት የታየ ሲሆን በዚህ ቀበሌን የማብቃት ተግባር በክልሉ 7 ሺህ 342 ቀበሌዎች ተደራጅተው 50 ሺህ የሰው ኃይል እንደተመደበላቸው ተጠቁሟል፡፡
ከዚህ ቀደም በወረዳዎች ተማክለው የነበሩ ሞያዊና አስተዳደራዊ አገልግሎቶች በቀበሌ ደረጃ በተገቢው የሰው ኃይል እየተሰጡ ይገኛሉ ተብሏል።
በተመሳሳይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) የወንጪ ደንዲ ኤኮ ሎጅ አካል የሆነው የደንዲ ክፍል ግንባታ የደረሰበትን ደረጃ ተመልክተዋል።
የሥራው የሲቪል ግንባታ ምዕራፍ ተጠናቅቆ አሁን የማጠናቀቂያ ሥራዎች በመሠራት ላይ መሆናቸው ነው የተገለጸው፡፡