የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ መርሐ ግብሮች ዛሬም ቀጥለው ይደረጋሉ
አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 25፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) የ35ኛ ሳምንት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ መርሐ ግብር ዛሬም ቀጥሎ ሲካሄድ አርሰናል ከበርንማውዝ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል፡፡
በፕሪሚየር ሊጉ ቀን 8 ሰዓት ከ30 በምሳ ሰዓት የጨዋታ መርሐ ግብር አስቶንቪላ ከፉልሃም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ፡፡
ቀን 11 ሰዓት ላይ ደግሞ ኤቨርተን ከኢፕስዊች ታውን እንዲሁም ከፕሪሚየር ሊጉ የተሰናበቱት ሌስተር ሲቲ እና ሳውዝሃምፕተን ይጫወታሉ፡፡
ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ አርሰናል በሜዳው ኤሚሬትስ ስታዲየም በርንማውዝን የሚያስተናግድበት ጨዋታ ይጠበቃል፡፡
መድፈኞቹ የሁለተኛነት ደረጃቸውን አስጠብቀው ሊጉን ለመጨረስ የዛሬውን ጨዋታ ማሸነፍ ይጠበቅባቸዋል፡፡
ትናንት በሜዳው ኢቲሃድ ስታዲየም ዎልቭስን ያስተናገደው ማንቼስተር ሲቲ 1 ለ 0 በማሸነፍ ከአርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ 3 ዝቅ በማድረግ 3ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡
በአቤል ንዋይ