በኦሮሚያ ክልል መዋዕለ ንዋያቸውን ለሚያፈሱ ባለሃብቶች አስፈላጊው ድጋፍ ይደረጋል
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 23፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ ዘርፎች መዋዕለ ንዋያቸውን ለሚያፈሱ ባለሃብቶች አስፈላጊው ድጋፍ ይደረጋል አሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ።
በኦሮሚያ ክልል የሚገኙ የኢቨስትመንት አማራጮችን ለባለሃብቾች ለማስተዋወቅ ያለመ የክልሉ ኢንቨስትመንት ፎረም በአዲስ አበባ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።
በፎረሙ ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ፣ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል፣ የኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን (ዶ/ር) እና ባለሃብቶች ተገኝተዋል።
ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ በዚህ ወቅት እንዳሉት÷ በኦሮሚያ ክልል ለተለያዩ ዘርፎች በርካታ የኢንቨስተመንት አማራጮች አሉ።
በክልሉ ያለውን እምቅ የተፈጥሮ ሃብት ለማልማት በትኩረት እየተሰራ አንደሚገኝ ገልጸው÷ በተለያዩ ዘርፎች መዋዕለ ንዋያቸውን ለሚያፈሱ ባለሃብቶች አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግ ተናግረዋል።
የመሰረተ ልማት ዝርጋታ፣ የመሬትና ኃይል አቅርቦት እንዲሁም ሌሎች ተግዳሮቾችን ለመፍታት ይሰራል ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ÷ ባለሃብቶች እና አልሚዎች በክልሉ ያለውን እምቅ የተፈጥሮ ሃብት በመጠቀም ኢንቨስት እንዲያደርጉም ጥሪ አቅርበዋል።
አቶ መላኩ አለበል በበኩላቸው÷ ኢትዮጵያን በጠንካራ ኢኮኖሚ ላይ ለመገንባት በትኩረት መስራት ይገባል ብለዋል።
የኦሮሚያ ክልል በኢንቨስትመንት ዘርፍ በተለያዩ አካባቢዎች ያከናወናቸው ሥራዎች የሚበረታቱና አርአያ እንደሚሆኑም አንስተዋል።
ሰላምን ለማረጋገጥ ልማትን ማጠናከር ይገባል ያሉት ሚኒስትሩ፥ ለዚህም ባለሃብቶች ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በልማት ላይ ትኩረት እንዲያደርጉ ጠይቀዋል።
ባለፉት ዓመታት የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርምን ጨምሮ በርካታ የፖሊሲ ማሻሻያዎች መደረጋቸውን ጠቁመው÷ ይህም የኢንቨስትመንት ዘርፉን እንዳነቃቃ ተናግረዋል።
በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር መንግስት በትኩረትና በቁርጠኝነት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።
በመላኩ ገድፍ