ኢትዮጵያ ቡና የ100 ሺህ ብር ቅጣት ተጣለበት
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 24፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በኢትዮጰያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ጨዋታ የኢትዮጵያ ቡና ደጋፊዎች በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ባጠፉት ጥፋት ክለቡ የ100 ሺህ ብር ቅጣት ተላልፎበታል፡፡
ኢትዮጵያ ቡና ከወልዋሎ ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ጋር ያደረገውን የ32ኛ ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ጨዋታ ያለምንም ግብ ማጠናቀቁ ይታወሳል፡፡
በጨዋታው ወቅት የኢትዮጵያ ቡና ደጋፊዎች የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንትን፣ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማህበርን እና የኢትዮጵያ መድን አሰልጣኝን በስም በመጥራት አፀያፊ ስድብ ስለመሳደባቸው ሪፖርት ቀርቦበታል።
በዚህም ደጋፊዎቹ ላጠፉት ጥፋት ክለቡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ዲሲፕሊን መመሪያ ክፍል 3 ምዕራፍ 3 አንቀፅ 66 በተራ ቁጥር 4 (ሀ) መሰረት 100 ሺህ ብር እንዲከፍል የውድድር አመራርና ስነ-ስርዓት ኮሚቴ ወስኗል።
ሊጉን ኢትዮጵያ መድን በ63 ነጥብ ሲመራው ኢትዮጵያ ቡና በ55 እንዲሁም ባህር ዳር ከተማ በ48 ነጥብ 2ኛ እና 3ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ፡፡