Fana: At a Speed of Life!

የኢትዮጵያውያን የጋራ ዐሻራ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ በደለል እንዳይሞላ …

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 24፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በደለል እንዳይሞላ በተቀናጀ አግባብ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ እና የተፋሰስ ልማት ሥራ እየተከናወነ ነው አለ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ግብርና ቢሮ፡፡

በቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማትና አጠቃቀም ዳይሬክተር ፈቃዱ ደሳለኝ እንዳሉት፤ ግድቡ በሚያዋስናቸው ወረዳዎች ማኅበረሰቡን በማሳተፍ የተፋሰስ ልማት እና የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው፡፡

በዚህም መሠረት የተለያዩ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም እና በሥነ ሕይወታዊ ዘዴ ችግኞች እየተተከሉ እንደሆነ ጠቅሰዋል፡፡

ለአብነትም በ2016/17 አረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ግድቡ በሚያዋስናቸው ወረዳዎች 44 ሚሊየን 51 ሺህ 173 ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በ22 ሺህ 263 ሔክታር ላይ መተከላቸውን አንስተዋል፡፡

የተተከሉት ችግኞች ዓይነትም፤ ለደን ልማት፣ ለደን ጥምር እርሻ አገልግሎት፣ የአፈር መከላትን ለመከላከል፣ ለምግብነት የሚውሉ ፍራፍሬዎች መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡

በችግኝ ተከላው ወቅት ከ595 ሺህ 780 በላይ የኅብረተሰብ ክፍሎች መሳተፋቸውን ለፋና ዲጂታል ተናግረዋል፡፡

ቀደም ሲል በተለያየ ምክንያት በከፍተኛ ሁኔታ የተራቆቱ መሬቶች መልሰው ማገገም መቻላቸው እና ከፍተኛ የአፈር መሸርሸር መቀነስ መቻሉ ከተከላው በኋላ የተገኙ ውጤቶች መሆናቸውንም ገልጸዋል፡፡

በቀጣይ በ2017/18 ዓ.ም የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብርም በተለይም ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በደለል እንዳይሞላ በ32 ሺህ 242 ሔክታር ላይ 55 ሚሊየን 417 ሺህ 500 ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እንደሚተከሉ ጠቁመዋል፡፡

በተጨማሪም በ48 ሺህ 61 ሔክታር የተራቆቱ አካባቢዎች ላይ የተፋሰስ ልማት እና የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራዎችን በተመረጡ የተለያዩ ቴክኖሎጅዎች የማልማት ሥራ ለመሥራት መታቀዱን ነው የገለጹት፡፡

በዮሐንስ ደርበው

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.