የአገልግሎት ጥራትን ለማሻሻል እየተሰሩ የሚገኙ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ – ዶ/ር መቅደስ ዳባ
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 6፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) የአገልግሎት ጥራትን ለማሻሻል እየተሰሩ የሚገኙ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ አሉ የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ።
የሚኒስቴሩና የክልል ጤና ቢሮ ከፍተኛ አመራሮች የጋራ ምክክር መድረክ በሀረር ከተማ እየተካሄደ ነው።
በመድረኩ የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር መቅደስ ዳባ በተጠናቀቀው የ2017 የበጀት ዓመት በጤናው ዘርፍ አበረታች ስራዎች መከናወናቸውን አንስተው÷ የጤና አገልግሎት ጥራትን በማሻሻል ረገድ እየተሰሩ የሚገኙ ተግባራትን ለማጠናከር ትኩረት ይሰጣል ብለዋል።
በቴክኖሎጂ የተደገፉ ስራዎች እውን በማድረግና በቅንጅት በመስራት የተገኙ ውጤቶችን ለማጎልበትና የታዩ ውስንነቶች ለመቅረፍ መረባረብ እንደሚገባም ተናግረዋል።
የሀረሪ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር አብዲ አሚን በበኩላቸው÷ በክልሉ አገልግሎትን በማሻሻል ረገድ አበረታች ውጤት መገኘቱን አንስተው፤ በቀጣይም ለሕዝቡ በቴክኖሎጂ የተደገፈና ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ ይሰራል ብለዋል።
ለሁለት ቀናት በሚካሄደው የጋራ ምክክር መድረክ በ2017 በጀት ዓመት የተከናወኑ ስራዎችን በመገምገም የቀጣይ አቅጣጫዎች የሚቀመጥበት መሆኑ ተገልጿል።
በተስፋዬ ኃይሉ