የኢትዮጵያ ወንጌል አማኞች አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል ለገና በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፈ
አዲስ አበባ፣ ታሕሣሥ 28፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የኢትዮጵያ ወንጌል አማኞች አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል ለኢየሱስ ክርስቶስ የገና በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፏል፡፡
የካውንስሉ ጠቅላይ ፀሐፊ ቄስ ደረጄ ጀምበሩ በዓሉን አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ÷ በኢትዮጵያና በተለያዩ ሀገራት ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የ2018 ዓ.ም የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በዓል የደስታና የፍቅር እንዲሆን ተመኝተዋል፡፡
የኢየሱስ ክርስቶስ መወለድ የእግዚአብሔርን ይቅር ባይነትና ለሰው ልጆች ያለውን ታላቅ ፍቅር የሚያሳይ መሆኑን አንስተዋል፡፡
በመሆኑም የወንጌል አማኞች በክርስቶስ ኢየሱስ በኩል የተሰጣቸውን ፍቅር ለሌሎች ማካፈል እንዳላባቸው አሳስበዋል።
ልዩነቶችን በእርቅ በመፍታት ለዘላቂ ሰላም እንትጋ ያሉት ቄስ ጀምበሩ÷ በተለይም የወንጌል አማኞች ፍቅርንና ሰላምን ከማወጅ ውጭ ሌላ መለኮታዊ ተልዕኮ የለንም ብለዋል።
በኢትዮጵያ የሚታዩ የልማት ስራዎች ችግሮችን በሰላማዊ መንገድ በመፍታት ለጋራ ጥቅም መስራት ከተቻለ በአጭር ጊዜ ውስጥ ከድህነት መውጣት የሚቻል መሆኑን አመላክተዋል፡፡
በመሆኑም የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በዓልን ስናከብር ለሌላቸው ወገኖች በማካፈል ሊሆን እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በሰለሞን በየነ