Fana: At a Speed of Life!

ውጤታማነትና ተጠያቂነትን መሰረት ያደረጉ የጤና ልማት ስራዎች…

‎አዲስ አበባ፣ ጥር 4፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ውጤታማነትና ተጠያቂነትን መሰረት ያደረጉ የጤና ልማት ስራዎች ተግባራዊ እየተደረጉ ናቸው አለ የክልሉ ጤና ቢሮ።

ቢሮው በክልሉ የጤና አገልግሎትን በመሰረታዊነት ማሻገር የሚያስችል የአቅም ግንባታ ስልጠና “ጠንካራ የአመራር ግንባታ ለውጤታማ የጤና ስርዓት” በሚል መሪ ሐሳብ ለዘርፉ አመራሮች እየሰጠ ይገኛል።
‎‎
የክልሉ ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ ሳሙኤል ዳርጌ በዚህ ወቅት እንዳሉት÷ ውጤታማነትንና ተጠያቂነትን መሰረት ያደረጉ የጤና ልማት ስራዎች በክልሉ ተግባራዊ እየተደረጉ ናቸው።
‎‎
‎የአቅም ግንባታ ስልጠናው የተጠናከረ የጤና ሥርዓት መፍጠር ላይ ያተኮረ መሆኑን አንስተው÷ ባለቤትነትን መፍጠርና ተጠያቂነትን ማረጋገጥ እንደሚገባ ተናግረዋል።

‎በክልሉ የጤናውን ዘርፍ ለማሻገር ተግዳሮት የሆኑ 15 ጉዳዮች በሳይንሳዊ ጥናት መለየታቸውን ጠቅሰው÷ ለዚህም 12 ስትራቴጂካዊ መፍትሄዎች በጥናቱ መቅረባቸውን ጠቁመዋል።

‎ስልጠናውም ከተደረገው ሳይንሳዊ ጥናት መነሻ መዘጋጀቱን አመላክተዋል።

‎በክልሉ የሕብረተሰቡን ተሳትፎ በማሳደግ በርካታ የጤና ልማት ስራዎች እየተሰሩ እንደሚገኙና የጤና ተቋማትን ዲጂታላይዝ በማድረግ አገልግሎቶቹ ከወረቀት ነጻ ለማድረግ የሚያስችሉ አበረታች ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን አስታውቀዋል።

‎ከዛሬ ጀምሮ ለስምንት ቀናት በሚሰጠው ስልጠና ከክልሉ ሁሉም መዋቅሮች የተወጣጡ የዘርፉ አመራሮች መሳተፋቸውን የቢሮ ኮሙኒኬሽን ለፋና ዲጂታል በላከው መረጃ አመላክቷል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.