የምዕራባውያንን ዘመናዊ የቅኝ ግዛት ፍላጎት የሚቃወም ሰላማዊ ሰልፍ የፊታችን ሰኞ በፕሪቶሪያ ይካሄዳል
አዲስ አበባ፣ ህዳር 18፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የምዕራባውያን አገራት በአፍሪካ ላይ ዘመናዊ የቅኝ ግዛት ፍላጎታቸውን ለመጫን የሚያደርጉትን ጥረት የሚቃወም ሰልፍ የፊታችን ሰኞ በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ከተማ ይካሄዳል።
ሰልፉን ያዘጋጁት የተባበሩት የኢትዮጵያ ማህበረሰብ ማህበር በደቡብ አፍሪካ እና የአፍሪካ ዳያስፖራ ፎረም ናቸው።
የተባበሩት የኢትዮጵያ ማህበረሰብ ማህበር በደቡብ አፍሪካ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር ሙላቱ ፈቃዱ ሰልፉ ሰኞ ሕዳር 20 ቀን 2014 ዓ.ም በኢትዮጵያ የጊዜ አቆጣጠር ከጠዋቱ 3 ሰዓት ጀምሮ በፕሪቶሪያ ከተማ በሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲና የአውሮፓ ሕብረት መስሪያ ቤት እንደሚካሄድ ለኢዜአ ገልጸዋል።
በሰልፉ ላይ የምዕራባውያን አገራት ኢትዮጵያን ጨምሮ በአፍሪካ ላይ ለመጫን የሚፈልጉትን ዘመናዊ የቅኝ ግዛት አስተሳሰብ የሚቃወሙ መልዕክቶች ይተላለፋሉ ብለዋል።
በሰልፉ ላይ በደቡብ አፍሪካ ዘጠኝ ግዛቶች የሚኖሩ ኢትዮጵያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን፣ ደቡብ አፍሪካውያንን ጨምሮ በአገሪቷ የሚኖሩ አፍሪካውያን ዜጎችና የፓን አፍሪካኒዝም አቀንቃኞች እንደሚሳተፉም ነው ፕሮፌሰር ሙላቱ የጠቆሙት።
በደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ስሪል ራማፖሳ የሚመራው የአፍሪካ ናሽናል ኮንግረስ (ኤኤንሲ)፣ በጁሊየስ ማሌማ የሚመራው የኢኮኖሚክ ፍሪደም ፋይተርስ ፓርቲን ጨምሮ ሌሎች በደቡብ አፍሪካ የሚገኙ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች በሰልፉ ላይ እንዲገኙ ጥሪ እንደቀረበላቸው አመልክተዋል።
“ኢትዮጵያ እየተዋጋች ያለችው ምዕራባውያን በአፍሪካ ላይ ለመጫን የሚፈልጉትን የኒኦ-ኮሎኒያኒዝም እሳቤ ነው” ያሉት ፕሮፌሰሩ ÷ በሰልፉ ላይ አፍሪካውያን ይሄን በመቃወም ከኢትዮጵያ ጎን መሆናቸውን እንደሚያሳዩ ተናግረዋል።
በአሁኑ ሰዓት አፍሪካውያን ኢትዮጵያ እያደረገች ያለችውን ትግል በመደገፍ ድምጻቸውን እያሰሙ እንደሚገኙም አመልክተዋል።
በፕሪቶሪያ ከተማ በሚገኙት የአሜሪካ ኤምባሲና የአውሮፓ ሕብረት መስሪያ ቤት ምዕራባውያን አገራት በኢትዮጵያ ላይ የሚያደርጉትን ጫናና በአፍሪካ ላይ የሚያራምዱትን ዘመናዊ የቅኝ ግዛት አስተሳሰብ እንዲያቆሙ የሚያሳስብ ደብዳቤ እንደሚሰጥም ተናግረዋል።
በደቡብ አፍሪካ የሚገኙ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ማህበረሰብ አባላት ሰልፎችን ከማድረግ ባለፈ በአገሪቷ ከሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ጋር በመሆን የዲፕሎማሲ ስራዎችን እያከናወኑ እንደሚገኝም ነው ፕሮፌሰር ሙላቱ ያስረዱት።
ሰኞ ሕዳር 20 ቀን 2014 ዓ.ም በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ከተማ የሚካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ አስተባባሪዎች አንዱ የሆነው የአፍሪካ ዳያስፖራ ፎረም ከ35 የአፍሪካ አገራት የተወጣጡ ዳያስፖራዎችን ያቀፈ ድርጅት ነው።
አካባቢዎን ይጠብቁ!
ወደ ግንባር ይዝመቱ!
መከላከያን ይደግፉ!
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!