የኢትዮጵያ እና የቻይና ግንኙነት ጠንካራና የማይሰበር ነው- ዶክተር አብርሀም በላይ
አዲስ አበባ፣ መጋቢት 20፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮጵያ እና የቻይና ግንኙነት ጠንካራና የማይሰበር ነው ሲሉ የመከላከያ ሚኒስትር ዶክተር አብርሀም በላይ ገለጹ፡፡
የመከላከያ ሚኒስትሩ ዶክተር አብርሀም በላይ እና በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ሚስተር ዣኦ ዢዩኣን ጋር በቢሾፉቱ ከተማ በመጠናቀቅ ላይ የሚገኘው የመከላከያ ሪፈራል ሆስፒታል የሚያስፈልገውን ዘመናዊ የህክምና ላቦራቶሪ መሰረተ ልማት ለመገንባት የሚያስችል የስምምነት ሰነድ ተፈራርመዋል፡፡
በዚሁ ወቅት ዶክተር አብርሃም የኢትዮጵያ እና የቻይና ግንኙት ጠንካራና የማይሰበር መሆኑን ጠቅሰው፥ ስምምነቱ የሆስፒታሉን ደረጃ ከፍ ያደርጋል ብለዋል።
አምባሳደር ዣኦ ዢዩኣን በበኩላቸው÷ የኢትዮጵያና የቻይና የሁለትዮሽ ግንኙነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል፡፡
ዘመናዊ የህክምና ላቦራቶሪ መሰረተ ልማት ለማቅረብና ለመገንባት እና የጋራ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ቻይና ትሰራለች ማለታቸውን ከመከላከያ ሰራዊት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።