አዲስ አበባ፣ መስከረም 25፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የሐረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ በኢትዮጵያ ከኔዘርላንድስ አምባሳደር ሄንክ ጃን ቤከር ጋር ተወያይተዋል።
በውይይታቸውም አቶ ኦርዲን የኔዘርላንድስ መንግስት በክልሉ የንፁህ መጠጥ ውሃ አቅርቦትን ለማጎልበት እየሰራቸው የሚገኙ ስራዎችን አድንቀዋል።
በተለይም በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ለሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች የንፁህ መጠጥ ውሃ ተደራሽ ለማድረግ እያከናወናቸው ለሚገኙ ተግባራት ምስጋና አቅርበዋል፡፡
በቀጣይም በፋይናንስ፣ በአቅም ግንባታና በቁሳቁስ እያደረጋቸው የሚገኙ ድጋፎችን አጠናክሮ እንዲቀጥል መጠየቃቸውን ከክልሉ ኮሙኒኬሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።
አምባሳደር ሄንክ ጃን ቤከር በበኩላቸው÷ የኔዘርላንድስ መንግስት በክልሉ የመጠጥ ውሃ አቅርቦትን ለማጎልበት እያከናወናቸው የሚገኙ ተግባራትን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡
የክልሉ መንግስት በራሱ እያካሄዳቸው ያሉ ስራዎችን እና የአመራሩን ቁርጠኝነት ያደነቁት አምባሳደሩ÷ኢትዮጵያና ኔዘርላንድስ ከፍተኛ የኢኮኖሚ አጋር መሆናቸውንም አንስተዋል፡፡