ቻይና በታይዋን ዙሪያ ወታደራዊ ልምምድ ጀመረች
አዲስ አበባ፣ መጋቢት 30፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የቻይና ጦር በዛሬው ዕለት በታይዋን አቅራቢያ ለሦስት ቀናት የሚቆይ ወታደራዊ ልምምድ መጀመሩን አስታወቀ፡፡
በልምምዱም የውጊያ ዝግጁነት ቅኝቶች እና ወታደራዊ ስልጠናዎች መካሄዳቸውን ሲ ጂ ቲ ኤን ዘግቧል፡፡
ልምምዱም “ታይዋን እና ውጫዊ ኃይሎች” ለሚያደርጉት ጠባጫሪ ድርጊት ከባድ ማስጠንቀቂያ መሆኑን የቤጂንግ ጦር ገልጿል፡፡
እንዲሁም በቻይና በኩል “የሉዓላዊነትና የግዛት አንድነትን ለማስጠበቅ ተገቢ እንቅስቃሴ” መሆኑ ተመልክቷል፡፡
የልምምዱ የመጀመሪያ ቀን ውሎ የተካሄደው÷ ከታይዋን ደሴት በስተሰሜን እና በደቡብ ታይዋን የባሕር ዳርቻ ዙሪያ እንዲሁም ከደሴቲቱ በስተምሥራቅ ባለው የአየር ክልል እና ባሕር ላይ ነው፡፡
የታይዋን መከላከያ ሚኒስቴርም በዛሬው ዕለት በደሴቲቱ ዙሪያ 42 የቻይና አውሮፕላኖች እና 8 መርከቦችን አግኝቻለሁ ማለቱን ጠቅሶ አር ቲ ዘግቧል፡፡
ልምምዱ የተጀመረው የታይዋን መሪ ጻይ ኢንግ ዌን ከአሜሪካ ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ኬቨን ማካርቲ እና ሌሎች የምክር ቤቱ እንደራሴዎች ጋር ተገናኝተው ከተመለሱ አንድ ቀን በኋላ ነው።