ኮርፖሬሽኑ በቂ ወታደራዊ ምርቶችን ለማምረት እየሠራ ነው
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 8፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የመከላከያ ሠራዊቱ አሥፈላጊ ትጥቅ ታጥቆ ሀገሩን እንዲጠብቅ ወታደራዊ ምርቶችን በበቂ መጠን ለማምረት እየተሠራ መሆኑን የመከላከያ ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽን አስታወቀ።
ኮርፖሬሽኑ የ2015 በጀት ዓመት የሥራ አፈፃፀምና የ2016 ዕቅድ አተገባበር ዙሪያ ለሁለት ቀናት ሲያካሂድ የቆየውን የውይይት መድረክ አጠናቋል።
በመድረኩ በኮርፖሬሽኑ ሥር የሚገኙ ክፍሎች የሥራ ኃላፊዎች ዝርዝር ሪፖርት አቅርበው ሰፊ ውይይት ተካሂዶባቸዋል።
የመከላከያ ተቋም የጀመራቸውን የሪፎርም አሠራሮችን ተግባራዊ በማድረግና ለሥራ እንቅፋት የሆኑ ጉዳዮችን ከባለድርሻ አካላት ጋር ተነጋግሮ እየፈታ በአስተማማኝ መልኩ ወደ ምርት እንዲገባ መደረጉም ተመላክቷል።
ኮርፖሬሽኑ ፥ አደናቃፊ አሰራሮችን በመቀየርና የሠው ኃይሉን በማዘመን እንዲሁም ያሉትን አድሶ ወደ ሥራ በማሥገባት በሚሊየን ይገባ የነበረውን ገቢ በቢሊየኖች መቀየር መቻሉም ተነስቷል።
በዚህም ሠራዊቱ አሥፈላጊ ትጥቅ ታጥቆ ሀገሩን እንዲጠብቅ ወታደራዊ ምርቶችን በበቂ ሁኔታ ለማምረት እየተሠራ እንደሚገኝ የገለፁት የመከላከያ ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽን ዋና ዳይሬክተር ጌታቸው ኃ/ማሪያም ናቸው፡፡
አክለውም ዋና ዳይሬክተሩ ፥ በአፍሪካ ግንባር ቀደምና ተፅዕኖ ፈጣሪ መሆን የቀጣይ የቤት ሥራዎቻችን ናቸው ማለታቸውን ከመከላከያ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።
አሁን ላይ ኮርፖሬሽኑ ገቢውን በማሳደግ፣ ተጓዳኝ የግብርና ሥራዎችን በመከወንና ግዙፍ ማሽኖችን በመግዛት የተሰጠውን ተልዕኮ በትጋት ለመፈፀም ከፍተኛ ርብርብ እያደረገ እንደሚገኝም ነው ያነሱት።
በየደረጃው ያሉ የኮርፖሬሽኑ አመራርና አባላትም ከውይይት መድረኩ ብዙ ግብዓቶችን እንዳገኙና ሀገር በምትፈልገው ልክ ለመሥራት መዘጋጀታቸውን ገልፀዋል።
#Ethiopia
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/fana_television/
ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!