በድሬዳዋ ለተመዘገቡ ታሪካዊ ቅርሶች ዕውቅና ተሠጠ
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 24፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ለሚገኙ 56 የተመዘገቡ ታሪካዊና ጥንታዊ ቅርሶች ዕውቅና ተሰጥቷል፡፡
ዕውቅና የተሠጠው በኢትዮጵያ ቅርስ ጥበቃ ባለሥልጣንና በአስተዳደሩ የባሕልና ቱሪዝም ቢሮ አማካኝነት ነው፡፡
ዕውቅና ከተሰጣቸው ቅርሶች መካከልም÷ ጥንታዊ አብያተ ክርቲያናትና መስጂዶች፣ ታሪካዊ ሲኒማ ቤቶችና መካነ መቃብሮች፣ ዋሻዎች እንዲሁም ዕድሜ ጠገብ መኖሪያ ቤቶችና ትምህርት ቤቶች ይገኙበታል፡፡
በመርሐ-ግብሩ ላይ የኢትዮጵያ ቅርስ ጥበቃ ባለሥልጣን ም/ዳይሬክተር ሕይወት ኃይሉ እንደተናገሩት÷ ጥንታዊና ታሪካዊ ቅርሶችን የመጠበቅና የመንከባከብ ኃላፊነት ለአንድ ተቋም ብቻ የሚተው አይደለም፡፡
በመሆኑም ቅርሶችን ተጠብቀው ለቀጣዩ ትውልድ እንዲተላለፉ ማድረግ የሁሉም ዜጋ ኃላፊነት ነው ብለዋል፡፡
ከዚህ አኳያ በድሬዳዋ ቅርሶችን በመጠበቅ ረገድ እየተሠራ ያለው ሥራ አበረታች መሆኑንና አስተዳደሩም የቱባ ባሕልና የቅርሶች መገኛ መሆኑን አንስተዋል፡፡
የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር በበኩላቸው ድሬዳዋ በተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ ቅርሶች የታደለች እንደሆነች ጠቅሰው÷ ለጎብኚዎች መዳረሻ ለማድረግም የመሰረተ ልማቶችን ለማሟት የተለያዩ ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
በመቅደስ ደረጀ