በአዲሱ ዓመት በተሰማራንበት መስክ ውጤታማ ለመሆን መትጋት አለብን – አቶ አወል አርባ
አዲስ አበባ፣ ጳጉሜን 4፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በአዲሱ ዓመት በተሻለ መነሳሳት በተሰማራንበት መስክ ውጤታማ ለመሆን መትጋት አለብን ሲሉ የአፋር ክልል ርዕሰ-መስተዳድር አወል አርባ ተናገሩ።
የአምራችነት ቀን “ከሸማችነት ወደ አምራችነት” በሚል መሪ ሃሳብ በተለያዩ መርሐ-ግብሮች በመላው የኢትዮጵያ ክፍል እየተከበረ ነው።
ቀኑን ምክንያት በማድረግም የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ እና የክልሉ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች በዱብቲ ወረዳ የሙዝ ችግኝ ተክለዋል።
ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት ፥ አምራችነትን በተለያዩ የሙያ መስኮች ማስቀጠል ይኖርብናል ማለታቸውን የዘገበው ኢዜአ ነው።
በአዲሱ ዓመትም በተሻለ መነሳሳት በተሰማራንበት መስክ ውጤታማ ለመሆን መትጋት አለብንም ነው ያሉት።
የእምራችነት ቀንን ምክንያት በማድረግ ዛሬ በ20 ሄክታር መሬት ላይ 4 ሺህ 800 የሙዝ ችግኞች መተከላቸውንና በአዲሱ ዓመትም በዚሁ መሬት ላይ 20 ሺህ የሙዝ ችግኞች ለመትከል መታሰቡን ተናግረዋል።
በአዲሱ ዓመት በትኩረት በመስራት ምርታማነትን ለማሳደግ ሁሉም በየደረጃው መሳተፍ እንደሚኖርበትም ነው የጠቆሙት።
ርዕሰ መስተዳድሩ አክለውም ፥ ባለሃብቶች ወደ አፋር ክልል መጥተው በተለያዩ የልማት ዘርፎች እንዲሳተፉ ጥሪ አቅርበዋል።