በ“የመደመር ትውልድ” መጽሐፍ ሽያጭ በሚለማው የጢያ ዓለም አቀፍ መካነ-ቅርስ ዲዛይን ላይ ውይይት ተካሄደ
አዲስ አበባ፣ መጋቢት 16፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሥራ በሆነው “የመደመር ትውልድ” መጽሐፍ ሽያጭ ገቢ በሚለማው የጢያ ዓለም አቀፍ መካነ-ቅርስ ፕሮጀክት ዲዛይን ላይ በሆሳዕና ከተማ ምክክር ተደርጓል፡፡
በመድረኩም÷ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መሥተዳድር እንዳሻው ጣሰውን ጨምሮ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ የክላስተር አስተባባሪዎች፣ የመካነ-ቅርሱ የቦርድ አባላት እና አማካሪ ድርጅቶች ተሳትፈዋል፡፡
አቶ እንዳሻው በዚሁ ወቅት እንዳሉት÷ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት “የመደመር ትውልድ” ከተሰኘው መጽሐፋቸው ሽያጭ በሚገኘው ገቢ የጢያ ዓለም አቀፍ መካነ-ቅርስን ለማልማት እየተሠራ ነው፡፡
ቀደም ሲልም መካነ-ቅርሱን ለማልማት የሀብት ማሰባሰብ ሥራ መከናወኑን አስታውሰዋል፡፡
አሁን ላይም የቦርድ አመራሮች ተሰይመው ሥራቸውን የሚጀምሩበት ወቅት ላይ ናቸው ማለታቸውን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ መረጃ አመላክቷል፡፡
የጢያ ዓለም አቀፍ መካነ-ቅርስን ማስተዋወቅ፣ ማልማት እና ከዘርፉ የሚገኘውን ሀብትም ማሳደግ እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡