ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን እያካሄደ ባለው የምክክር ምዕራፍ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት
• ግንቦት 21 ቀን 2016 ዓ.ም ከ2 ሺህ በላይ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን በመወከል የሚሳተፉ ተሳታፊዎች በዓድዋ ድል መታሰቢያ አዳራሽ ተገኝተው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የምክክር ምዕራፍ ጀምረዋል፡፡
• ከግንቦት 21 ቀን 2016 ዓ.ም ግማሽ ቀን በኋላ ተሳታፊዎች በየሕብረተሰብ ክፍሎቻቸው በመሆን ከየማህበረሰብ ክፍሎቻቸው በአደራ ያመጧቸው የአጀንዳ ሀሳቦች ላይ ውይይት በማድረግ ላይ ናቸው፡፡
• ዛሬ ግንቦት 22 ቀን 2016 ዓ.ም በየህብረተሰብ ክፍሎቻቸው ውይይቶችን ሲያደርጉ የነበሩት ተወካዮች የሚስማሙባቸውን የአጀንዳ ሀሳቦች በየማህበረሰብ ክፍሎቻቸው በቃለ-ጉባኤ አስደግፈው ለኮሚሽኑ ያቀርባሉ፡፡
• ተወካዮች በአጀንዳ ሃሳቦቻቸው ላይ ከተወያዩ በኋላ በቀጣይ የምክክር መድረኮች ሀሳቦቻቸውን በውክልና የሚያቀርቡላቸውን 121 ተወካዮችን የሚመርጡ ሲሆን÷ ይህም እስከ ግንቦት 23 ቀን 2016ዓ.ም እንደሚቀጥል ይጠበቃል፡፡
• ከላይ ባለው መድረክ በትይዩ ነገ ግንቦት 23 ቀን 2016 ዓ.ም የፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች፣ መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት እና ማህበራት ተወካዮች፣ ከሶስቱ የመንግስት አካላት የተወከሉ ተወካዮች እንዲሁም ተፅዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦች በዓድዋ ድል መታሰቢያ አዳራሽ የሚገናኙበት መድረክ ይኖራል፡፡
• በመድረኩ እነዚህ ባለድርሻ አካላት እርስ በእርስ የሚተዋወቁባቸው ሁነቶች ይኖራሉ፡፡ በተጨማሪም እየተካሄደ ስላለው የምክክር ምዕራፍ አስፈላጊው ገለጻ እና ማብራሪያ በኮሚሽኑ ይሰጣቸዋል፤ በቀጣይ ስለሚጠበቁባቸው ስራዎች ግንዛቤን የሚፈጥር መርሃ-ግብር እንደሚዘጋጅላቸውም የኮሚሽኑ መረጃ አመላክቷል።