የቤተ-መንግሥት አሥተዳደርና የፕሬዚዳንት ጽ/ቤት ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው ሠራተኞች ማዕድ አጋሩ
አዲስ አበባ፣ ጳጉሜን 4፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የቤተ-መንግሥት አሥተዳደርና የፕሬዚዳንት ጽሕፈት ቤት የኅብር ቀንን በማስመልከት ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው ሠራተኞች ማዕድ አጋሩ፡፡
የኅብር ቀን ”ኅብራችን ለሰላማችን” በሚል መሪ ሐሳብ በሀገር አቀፍ ደረጃ በተለያዩ ሁነቶች እየተከበረ ሲሆን÷ የማዕድ ማጋራቱ የተከናወነውም ዕለቱን በማስመልከት ነው፡፡
የቤተ-መንግስት አሥተዳደር ዋና ዳይሬክተር ምትኩ ደሬሳ÷ በተለይም በአዋሽ መልካሳና በቆቃ 200 ሔክታር መሬት ላይ የአሥተዳደሩ ሠራተኞችን በማስተባበር በተሠራው ሥራ ውጤት ተገኝቷል ብለዋል።
አሥተዳደሩ በበጋ መስኖ ያለማውን ስንዴ ዝቅተኛ ደመወዝ ላላቸው ሠራተኞች ድጋፍ ማድረጉን ገልጸው÷ ይህ የሁሉም ሠራተኞች የጋራ ትብብር ውጤት መሆኑን ለኢዜአ ገልጸዋል፡፡
በቀጣይም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ከአሥተዳደሩ ሠራተኞች በተጨማሪ ዝቅተኛ ደመወዝ ለሚከፈላቸው የመንግሥት ሠራተኞች ለማቅረብ እንደሚሠሩ አመልክተዋል።