በአማራ ክልል ያልተቋጨውን ሕግ የማስከበር ሥራ ለማጠናቀቅ ዝግጅት ተደርጓል ተባለ
አዲስ አበባ፣ የካቲት 22፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በአማራ ክልል ያልተቋጨውን ሕግ የማስከበር ሥራ ለማጠናቀቅ ዝግጅት መደረጉን የክልሉ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት አስታወቀ፡፡
የክልሉ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት”ቀበሌዎቻችንን በማጽናት ሁለንተናዊ እምርታ እናስመዘግባለን” በሚል መሪ ሃሳብ ለከተማ እና ገጠር ቀበሌያት አመራሮች ስልጠና እየሰጠ ነው፡፡
በስልጠናው የአማራ ክልል ርዕሰ መሥተዳድር አረጋ ከበደ ባስተላለፉት መልዕክት ÷በአማራ ክልል በአሁኑ ወቅት ከ4 ሚሊየን በላይ ተማሪዎች ከትምህርት ገበታ ውጪ መሆናቸውን አንስተዋል፡፡
ስለሆነም የቀበሌ አመራሮች ተማሪዎች ወደ ት/ቤት እንዲመለሱ በትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባ ነው ያሳሰቡት፡፡
መንግሥት ለግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚ ልዩ ትኩረት በመስጠት ከፍተኛ የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን ጠቁመው÷ የአፈር ማዳበሪያን ጨምሮ በድጎማ የተገዙ የግብርና ግብዓቶች ወደ ቀበሌዎች እንዲደርሱ መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡
የአማራ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ሃላፊ ይርጋ ሲሳይ በበኩላቸው ÷ብልጽግና በብዙ መስዋዕትነት የተወለደ ፓርቲ መሆኑን ገልፀው፤ለውጡ በብልሃት እና በቅንጅት በመመራቱ ባለፉት 6 ዓመታት በርካታ ስኬቶች መመዝገባቸውን ጠቅሰዋል፡፡
አሳታፊ እና ኀብረ ብሔራዊ የሆነው ብልጽግና ፓርቲ በችግር እና ተጽዕኖ ውስጥ ሆኖም የልማት እና የመልካም አስተዳደር ስኬቶችን አስመዝግቧል ያሉት ሃላፊው÷የልማት ተግዳሮት በሆኑ ሃይሎች ላይ ግን ሕግ የማስከበሩ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡
በዛሬው እለት የተጀመረው የቀበሌ አመራሮች ስልጠና በክልሉ በሁሉም ዞኖች፣ ከተማ አሥተዳደሮች እና ቀበሌዎች የሚሰጥ ሲሆን÷ስልጠኛው ለ3 ተከታታይ ቀናት ይቆያል መባሉን የክልሉ ኮሙኒኬሽን መረጃ አመላክቷል፡፡